Monday, February 26, 2018

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ዝርዝር የአፈፃፀም መመሪያ

(Feb 26, (ኢትዮጵያ ))--(የሚኒስትሮች ምክር ቤት ባሳለፍነው የካቲት 9 ቀን ለስድስት ወራት የሚቆይ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማወጁ ይታወሳል። በዚህም መሰረት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ኮማንድ ፖስት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ዝርዝር የአፈፃፀም መመሪያ የካቲት 14 ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ ሙሉ መመሪያውን እንደሚከተለው አቅርበነዋል።

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መመሪያ ቁጥር አንድ
ክፍል አንድ፦የተከለከሉ ተግባራት
ንዑስ ክፍል አንድ፦ በማንኛውም የአገሪቱ ክፍሎች የተከለከሉ ተግባራት

1) ህገ መንግስቱንና ህገ መንግስታዊ ስርዓቱን የሚጥስ ተግባር መፈጸም፣ በህገ መንግስቱና ህገ መንግስታዊ ስርዓቱ ላይ የሚፈጸሙ በወንጀል ህጉ ከአንቀጽ 238 እስከ 260 ድረስ የተመለከተ ማናቸውንም ወንጀሎች መፈጸም

2) የህዝቦችን መቻቻልና አንድነት የሚጎዳ ተግባር መፈጸም። ማንነትን፣ ዘርን፣ቋንቋን፣ ሃይማኖትን፣ የፖለቲካ አመለካከትን መሰረት ያደረገ ማንኛውንም አይነት በህይወት፣ በንብረት እንዲሁም አካላዊ ወይም ስነልቦናዊ ጥቃት መፈጸም ወይም ማፈናቀል፣ እነዚህን ድርጊቶች እንዲፈጸሙ መቀስቀስ ማነሳሳት

3) በአሸባሪነት ከተፈረጁ ድርጅቶች አመራሮች፣ አካላት እና ጸረ ሰላም ቡድኖች ጋር ማናቸውንም ግንኙነት ማድረግ፣የአሸባሪ ድርጀቶችን አላማ ማስፈጸም ጽሁፎችን መያዝ ማስተዋወቅ

4) የትራንስፖርት እንቅስቃሴ ማወክ፤ የተሽከርካሪ የባቡር እንቅስቃሴ ማወክ፣ የመንገድ ሃዲድ መዝጋት ጉዳት ማድረስና ሌሎች መሰል እንቅስቃሴ ማሳየትም ሆነ አገልግሎት ማስተጓጎል፣ ከተቀመጠው ታሪፍ በላይ ታሪፍ መጨመር የተከለከለ ስምሪት ማድረግ
5) የህዝብ አገልግሎት ማስተጓጎል ማቋረጥ፣ የህዝብ መገልገያዎች የንግድ ስራዎች ሱቆች የመንግስትም ሆነ የግል ተቋማት መዝጋት ወይም ምርትና አገልግሎት እንዲቋረጥ ማድረግ፣ ከስራ ቦታ ያለ በቂ ምክንያት መጥፋት ወይም ስራ ማቆምና ስራን መበደል
6) በመሰረተ ልማቶች ላይ ጉዳት ማድረስ፣ በህዝቦች፣ በመንግስት ተቋማትና የግል ንብረት ላይ በማንኛውም መንገድ ጉዳት ማድረስ

7) የህግ አስከባሪዎች ስራ ማወክ፣የህግ አስከባሪዎች የሚሰጡትን ማንኛውንም ትዕዛዝ አለማክበር፣ ስራቸውን አለማክበር፣ ለፍተሻ አለመተባበር፣ ወይም እንዲቆሙ ሲጠየቁ አለመቆም፣ ኬላዎችን ጥሶ ማለፍ፣ የህግ አስከባሪዎች ላይ ጥቃት መፈጸም ወይም ለመፈጸም መሞከር ስራቸውን ማዛባት፣እስረኞችን ወይም የህግ ታራሚዎችን ማስፈታት ወይም እንዲያመልጡ ማድረግ
8) ያልተፈቀደ ሰልፍ፣ የአደባባይ ስብሰባ፣ የህዝብና የዜጎች ሰላምና ጸጥታ ለማስከበር ሲባል ከኮማንድ ፖስቱ ፍቃድ ውጪ ማናቸውንም ሰልፍና የአደባባይ ስብሰባ ማድረግ

9) በትምህርት ተቋማት አድማ ማድረግ ፣በትምህርት ቤቶች፣ በዩኒቨርሲቲዎችና በሌሎች ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የመማር ማስተማር ሂደቶችን የማወክ፣ አድማ ማድረግ፣ የትምህርት ተቋማትን መዝጋት፣ እንዲዘጉ ቅስቀሳ ማድረግ ወይም የትምህርት ማህበረሰቡ ላይ ጉዳት ማድረስ የተከለከለ ነው።

10) በስፖርት ማዘውተሪያዎች አድማ ማድረግ በስፖርት ማዘውተሪያዎች ማዕከላት ከስፖርት ተግባር ውጪ የሆኑ ሁከቶችና ብጥብጦችን መፍጠር የተከለከለ ነው።

11) ሁከትና ብጥብጥ የሚያነሳ ቅስቀሳና ግንኙነት ማድረግ:-
ማንኛውም ሁከት ብጥብጥና በህዝቦች መካከል መጠራጠር መፍጠር፣ አድማና ህገ-ወጥ ተግባር መፈጸም ወይም እንዲፈጸም የሚያነሳሳ ይፋዊም ሆነ ድብቅ ቅስቀሳ በማናቸውም በኩል ማድረግ ጽሁፍ ማዘጋጀት፣ ማተምና ማሰራጨት፣ ትዕይንት ማሳየት፣ በምልክት መግለጽ ወይም መልዕክት በማናቸውም ሌላ መንገድ መግለጽ፣ ይፋ ማድረግ፣ ፍቃድ ሳይኖር ማንኛውንም ህትመት ወደ አገር ውስጥ ማስገባት ወይም ወደ ውጭ አገር መላክ፣ በሞባይል፣ በጽሁፍ፣ በቴሌቪዥን በሬድዮ፣ በማህበራዊ ሚዲያ ወይም ሌሎች የግንኙነት ዘዴዎች መለዋወጥ የተከለከለ ነው።

12) መሰረታዊ ሸቀጥ ዝውውር ማድረግ በመሰረታዊ ሸቀጦች አቅርቦት፣ ዝውውርና ስርጭት ማወክ የተከለከለ ነው።

13) ባህላዊ፣ ህዝባዊና ሃይማኖታዊ በዓላትን ማወክ:-
ባህላዊ፣ ህዝባዊና ሃይማኖታዊ ብሄራዊ በዓላት ላይ በማንኛውም ሁኔታ ማወክ፣ ማደናቀፍ ወይም ከበዓሉ ጋር የማይገናኙ ድርጊቶች መፈክሮችን በማንኛውም መንገድ ማስተጋባት የበዓሉ ተሳታፊዎች ላይ የህይወት የሃይል ድርጊት ወይም ዛቻ መፈጸም፣ በህዝቦች መካከል መቃቃርና መጠራጠርን እንዲሁም ስጋትን የሚፈጥሩ ሁከት ብጥብጥ የሚያነሳሳ ቅስቀሳ ማድረግ የተከለከለ ነው።

14) የጦር መሳሪያ ይዞ መገኘት:-ማናቸውም የጦር መሳሪያ፣ ስለት ወይም እሳት የሚያስነሱ ነገሮችን ወደ ገበያ፣ የሃይማኖት ተቋማት ወይም ወደ ማናቸውም ህዝብ የተሰበሰበበት ቦታ ይዞ መግባት የተከለከለ ነው።

15) ትጥቅን በሶስተኛ ሰው እጅ እንዲገባ ማድረግ፤ ማናቸውም የህግ አስከባሪ አካላት

16) የህዝብን ሰላምና ጸጥታ ለማደፍረስ ድጋፍ ማድረግ ፣ህገ-ወጥ ድርጊት የሚፈጽሙ ሰዎችን በማናቸውም መንገድ መደገፍ፣ ከለላ መስጠት፣ መደለያ መስጠት፣ ማብራራት የተከለከለ ነው።

17) በጸጥታ ጉዳይ ላይ መግለጫ መስጠት አስቸኳይ ጊዜ ኮማንድ ፖስት ፍቃድ ውጭ በጸጥታ ጉዳይ ላይ የፌደራል መንግስት፣ የክልል አካል ወይም ሃይል በህዝብ ይፋ የሚሆን መግለጫ መስጠት የተከለከለ ነው።

18) በአዋጁና አዋጁን ለማስፈፀም የወጡ መመሪያዎችን ማደናቀፍ የአስቸኳይ አዋጅና አዋጁን ለማስፈፀም የወጡ መመሪያዎች በማጥላላት በመቃወም ላይ ያተኮሩ መረጃዎች በማሰራጨት ወይም ማንኛውንም መሰል ድርጊቶች መፈፀም ክልክል ነው።

ንዑስ ክፍል ሁለት
የተወሰኑ አካባቢዎች እንዳይፈጸሙ የተከለከሉ ተግባራት
ክፍል አንድ ስር የተዘረዘሩት እንደተጠበቀ ሆኖ ኮማንድ ፖስቱ የሚወስነው ቦታ ላይ ተግባራዊ ይሆናል።

19) የጦር መሳሪያ ይዞ መንቀሳቀስ
ማንኛውንም የጦር መሳሪያ ስለት ወይም እሳት የሚያስነሱ ነገሮችን ከይዞታው ውጪ ይዞ መንቀሳቀስ የተከለከለ ነው።

20) የሰዓት እላፊ እገዳ፣የልማት አውታሮች መሰረተ ልማትና የኢንቨስትመንት ተቋማት በፋብሪካዎች በመሰል የልማት ተቋማት ወይም በመኖሪያ አካባቢ ኮማንድ ፖስቱ በሚወስነው ጊዜ ከተፈቀደለት ሰዓት በስተቀር መንቀሳቀስ ክልክል ነው።
በተከለከሉ ቦታዎች ላይ ሰዓት እላፊውን ተላልፎ የተገኘ ማንኛውም ሰው ላይ እርምጃ እንዲወስዱ ስልጣን ተሰጥቷል።

21) ሁከትና ብጥብጥ ለማስቆም አደጋ ለመከላከል የሚደረግ እንቅስቃሴን ማወክ፣
ሰላምና ፀጥታን በተመለከተ የሚጠረጠሩ ሰዎችን ወይም ቡድኖችን ወደተወሰነ አካባቢ እንዳይወጡ ይደረጋል
ወደ ተዘጋ መንገድ ወደ ተከለከለ አካባቢ ኮማንድ ፖስቱ ያስቀመጠውን እገዳ መተላለፍ የተከለከለ ነው።


ክፍል ሦስት
የመተግበር ግዴታ

22) የተከራይ መረጃ መያዝና የማስታወቅ ግዴታ
ማንኛውንም ቤት አከራይና ሌሎች ነገሮችን የሚያከራይ ግለሰብ ወይንም ድርጅት የተከራዩን ዝርዝር መረጃ በመያዝ በ24 ሠዓት ውስጥ ለፖሊስ አካል የማሳወቅ ግዴታ አለበት፣ በተጨማሪም የውጭ አገር ዜጋ ከሆነ የፓስፖርቱን ቪዛ ኮፒ በመያዝ በአቅራቢያው ላለ ፖሊስ ጣቢያ የማሳወቅ ግዴታ አለበት።

23) መረጃ የመስጠት ግዴታ
ሰላም ለማስፈን ሲባል ማንኛውም አካል በየደረጃው ያሉ የህግ አስፈጻሚ አካላት መረጃ ሲጠይቁ የመስጠት ግዴታ አለበት።

24) የህግ አስፈጻሚ አካላት የአስቸኳይ ጊዜ ኮማንድ ፖስቱ የተዋረዱ የእዝ ሰንሰለቱን ተከትሎ ይዋቀራል፤ ለዚህም የሎጂስቲክና የግብዓት አቅርቦት በሚወስነው መሰረት የመፈጸም ግዴታ አለባቸው፤ የሚወሰደው እርምጃ የአስቸኳይ ጊዜ እርምጃ የማክበር የመተባባር ግዴታ አለባቸው።

25) ስልጣን ባለው አካል የሚወሰዱ የአስቸኳይ ጊዜ እርምጃዎች ከላይ የተጠቀሱ ክልከላዎች ተላልፎ የተገኘ ወይንም ለአዋጁ መውጣት መንስኤ የሆኑ ሕገ-መንግሥታዊ ስርዓቱን የመናድ ወንጀሎችን፣ አዋጁ ከወጣ በኋላ ህገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን በመጣስ የተፈጸሙ ወንጀሎችን፣ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አንቀጽ 15 የተመለከቱትን በመተላለፍ የተፈጸሙ ወንጀሎች ወይንም ከነሱ ጋር ተያያዥ ወይንም ተቀራራቢ የሆኑ የወንጀል ድርጊቶችን ለፈጸሙ ዲፕሎማቶችና ልዩ መልዕክተኞች በዋና ወንጀል አድራጊዎች ላይ ትኩረት አድርጎ እርምጃ እንዲወሰድ ስልጣን ተሰጥቶታል።

26) ስለሚወሰዱ እርምጃዎች ከላይ የተጠቀሱት ክልከላዎችን ተላልፎ የተገኘ ሕገ መንግሥቱንና ህገ መንግሥታዊ ስርዓቱን በመተላለፍ በተገኘ ማንኛውም ሰው ላይ የህግ አስከባሪዎች
1. ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ በቁጥጥር ሥር ማዋል
2. አዋጁ እስከሚያበቃ ድረስ ኮማንድ ፖስቱ በሚወስነው እንዲቆይ ማድረግ
3. ተገቢውን የተሃድሶ ትምህርት በመስጠት፣ የሚለቀቀው እንዲለቀቅ፣ ወደ ፍርድ ቤት የሚቀርበው በህጉ መሰረት እንዲቀርብ ማድረግ
4. ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ በማናቸውም ጊዜ ብርበራ ማድረግ የአካባቢውን ህዝብና ፖሊስ ማሳተፍ፣ ማንኛውንም ወንጀል የተፈጸመበትን ወይም ሊፈጸምበት የሚችለውን ንብረት መያዝ፣ ባለበት እንዲጠበቅ ማድረግ
5. የተዘረፉ ንብረቶችን በማጣራት ለባለቤቶቹ እንዲመለሱ ማድረግ
6. በትምህርት ተቋማት ሁከትና ረብሻ ተሳትፎ በሚያደርጉ ተማሪዎችና ሰራተኞች ላይ ህጋዊ እርምት መውሰድ፣ አስተዳደራዊ እርምጃ እንዲወሰድ ለተቋማቱ ትዕዛዝ መስጠት
7. ማንኛውንም የህዝብን ሰላምና ጸጥታ ሊያደፈርሱ ይችላሉ ወይም ለጉዳት ተጋላጭ ይሆናሉ ተብለው የሚጠረጠሩና የሚታሰቡ ሰዎችን ቡድኖችን ወደ ተወሰኑ አካባቢ እንዳይገቡ፣ እንዲወጡ እንዳይገኙ ወይም በተወሰነ አካባቢ ብቻ እንዲቆዩ ማድረግ እና
8 .ሌሎች አግባብነት ያላቸውን እርምጃዎችን መውሰድ ይችላሉ

27) ማጣራትና መለየት:-
1. የአስቸኳይ ጊዜ ኮማንድ ፖስቱ በቁጥጥር ስር ከሚያውላቸው ተጠርጣሪዎች የተሃድሶ ትምህርት ተሰጥቷቸው የሚለቀቁ በዋና ወንጀል አድራጊነት በአባሪነት የሚጠየቁና የሚለቀቁ ሰዎች የሚጣሩበትንና የሚለዩበትን መስፈርቶች ያወጣል።
2. የሚመለከታቸው የህግ አስከባሪ አካላት በመስፈርቱ መሰረት ተጠርጣሪዎች ይለያሉ፤ በአንቀጽ 24 መሰረት ተገቢውን ቅጣት ይፈጽማሉ

3 .ስልጣን ያላቸው አካላት አቃቤ ህግ የስራ ክፍሎች የህግ ተጠያቂነት ማረጋገጥ በሚያስችል ጉዳዮች ላይ በህግ መሰረት ስራዎችን ያከናውናሉ

28) ብርበራ የሚካሄድበት ሁኔታ
በዚሁ መመሪያ አንቀጽ 24 ንዑስ አንቀጽ 4 መሰረት አስከባሪ የህግ አባላት ብርበራ በሚያደርጉበት ጊዜ:

1. የመስሪያ ቤቱን መታወቂያ በማሳየት
2 .የመጡበትን አላማ ምርመራው ወይም ፍተሻው የሚካሄድበትን ምክንያት መግለጽ
3. የቤቱ ባለቤት ወይም ነዋሪ የብርበራ ሂደቱን እንዲከታተል መፍቀድ
4 .ብርበራው በሚካሄድበት ወቅት የአካባቢው ፖሊስና ህብረተሰብ አባላት እንዲገኙ ማድረግ

29) የሃይል አጠቃቀም
ህግ አስከባሪ አካላትና የድርጅት ጥበቃዎች አስቸኳይ ጊዜ አዋጁና መመሪያውን ለማስፈጸም የራሳቸውና የሰዎችን ህይወትና ንብረት በመጠበቅ አስፈላጊና ተመጣጣኝ ሃይል ሊጠቀሙ ይችላሉ።

30) በትምህርት ቤቶች፣ በዩኒቨርሲቲዎችና በሌሎች ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ውስጥ አድማ የሚያደርጉ ሰዎችን ለመያዝና ለማስቆም የህግ አስከባሪ አካላት በእነዚህ ተቋማት ውስጥ በመግባት አስፈላጊውን እርምጃ መውሰድ ይችላሉ። እንዲሁም በሌሎች የግልና የመንግስት ተቋማት ውስጥ አድማ የሚያደርጉ ሰዎች ለመያዝና ሰላምና ጸጥታን ለማረጋገጥ የህግ አስከባሪ አባላት በእነዚህ ተቋማት ውስጥ መግባት አስፈላጊ ከሆነ መቆየት ይችላሉ።
(ኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት)
Home

No comments:

Post a Comment