Wednesday, January 10, 2018

የግብፅና የኤርትራ ድብቁ ጋብቻ ቀጣናውን ወዴት ያመራዋል

(Jan 10, (አዲስ አበባ))--የግብፅ መከላከያ ሠራዊት ጦሩን በኤርትራ ስለማስፈሩ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ዘግበዋል። ይህ የግብፆች አካሄድ ለቀጣናው ብሎም በቅርብ ርቀት ላለቸው ኢትዮጵያ ያለው አንድምታ ብዙ ስለመሆኑ በጉዳዩ ዙሪያ ቅርበት ያላቸው ምሁራን ተናግረዋል።  በፌዴራሊዝም፣ ዳይቨርሲቲ ኤንድ ኮንፍሊክት ማኔጅመንት ሁለተኛ ዲግሪያቸውን የሠሩትና በደቡብ ሱዳን ለአራት ዓመታት በአማካሪነት የሠሩት አቶ ካህሳይ ገብረእየሱስ እንደሚናገሩት፤ የግብፅ ፖለቲከኞች በምዕራቡ ዓለም ያላቸው ተሰሚነት ቀንሷል።

ከዚህ በተቃራኒው የኢትዮጵያ የፖለቲካ ተሰሚነትና የኢኮኖሚ ዕድገት የምዕራቡንም ሆነ የምሥራቁን አገራት ቀልብ እየሳበ ነው። ስለሆነም የቀጣናውን ፖለቲካ የበላይነት አጥብቀው ስለሚፈልጉት ይሄንን ማድረጋቸው የሚጠበቅ ነው።

ኢትዮጵያ የአባይን ወንዝ ከኤሌክትሪክ ኃይል ባለፈ ለመስኖ ልትጠቀምበት እንደማትችል ብታውቅም በሙሉ መሬቷን በአባይ ልታለማ ለምትችለው ሱዳን ትልቅ ትምህርት ሰጥታለች። ይህም ለግብፅ ፖለቲከኞች ያልጠበቁትን ኪሳራ አምጥቶባቸዋል የሚሉት አቶ ካህሳይ፤ የኢትዮ- ሱዳን ግንኙነት እየተጠናከረ መምጣቱን በመገንዘብም ጭምር የፕሬዚዳንት አልበሽርን መንግሥት ለማስገልበጥ ግብፆቸ ኤርትራ በመግባት የሱዳን መንግሥት ተቃዋሚዎችን ማሰልጠን መጀመራቸውን ነው የገለጹት። በመቀሌ ዩኒቨርሲቲ የስትራቴጂክ ግንኙነት ማዕከል ዳይሬከተር ረዳት ፕሮፌሰር መርሳ ፀሐዩም ተመሳሳይ ሃሳብ ነው ያላቸው።

ግብፅ በኤርትራ ሳዋ ማሰልጠኛ እስከ 30ሺ ጦር የማስፈር ሃሳብ አላት፤ በኢትዮጵያና በሱዳን ላይ ጫና በማሳደርም ብሄራዊ ጥቅሟን ለማስከበር እየሠራች ነው። ከዚህ አንጻር በሱዳን ላይ መፈንቅለ መንግሥት ለማድረግ እየሠራች ነው ሲሉም ነው የግብፅን እንቅስቃሴ ያስረዱት።

 ከዚህም በተጨማሪ የአረቡ ዓለም የፖቲካ ትኩሳት ወደ ምሥራቅ አፍሪካ እየተሳበ መሆኑን በመጥቀስም፤ የኤርትራ መንግሥት የውጭ ግንኙነቱን መቆጣጠር የማይችልና የውጭ ግንኙነቱም ከነፈሰው ጋር የሚነፍስ በመሆኑ በአገር ግንባታ አገሪቱን ማስቀጠል አልቻለም፤ ስለሆነም ህልውናውን እስካስቀጠለ ድረስ ለሌሎች ድጋፍ ማድረግም ብቻ ሳይሆን ሌሎች ላቅ ያሉ ውሳኔዎችንም እስከማሳለፍ የሚደርስ ዕርምጃ ሊወስድ ይችላል ሲሉ ተናግረዋል። ግብፅ ደግሞ ይሄንን እንደመልካም አጋጣሚ ተጠቅማ እያጣች ያለውን የፖለቲካ የበላይነት ለማካካስ ቀጣናውን ሊያተራምስ የሚችል ዕርምጃ መውሰዷ አይቀርም፤ አሁን የሚታየው ምልክትም ያንን ያረጋግጣል ብለዋል፤ ረዳት ፕሮፌሰሩ።

 የፖለቲካ ምሁሩ አቶ ልደቱ አያሌው በበኩላቸው፤ በምሥራቅ አፍሪካ ቀጣና አዳዲስ የኃይል ሚዛን እንቅስቃሴዎች መኖራቸውን ያነሱና ለምሥራቅ አፍሪካ አካባቢ ቅርብ ያልሆኑ አገሮች ጭምር አካባቢውን እየተቆናጠጡ መሆናቸውን ለኢትዮጵያ ስጋት እንዳለው ይገልጻሉ። ግብፅ ወታደሮቿን በኤርትራ ማስገባቷ ኢትዮጵያ ለኤርትራ ቅርብ እንደመሆኗ ትልቅ ስጋት አለው ይላሉ።

«ግብፅ የሩቁንና የቅርብ ጥቅሟን በማየት ፊቷን ወደ አፍሪካ አዙራለች። ግብፆች በኢትዮጵያ መረጋጋት እንዳይኖር ለዘመናት ሲሠሩ ነው የኖሩት። አሁንም ይህን አጠናከረው እየሄዱበት መሆኑን እንቅስቃሴያቸው ያሳያል። በግብፅ ያለው መንግሥት ወታደራዊ በመሆኑና የወታደራዊ መንግሥት ባህሪ ደግሞ ስሜትን መቀስቅስ በመሆኑ የአባይን ጉዳይ ለዚህ እየተጠቀሙበት ነው» ሲሉም ነው አቶ ልደቱ የግብፅን እንቅስቃሴ የገለጹት።

 በግብፅና በሱዳን መካከል የነበረውን ግንኙነት የአባይ፣ የንግድ ግንኙነት ሲያቀዘቅዘው ነበር። አሁን ግን ሱዳን ጥቅሟን ለማስከበር ከኢትዮጵያ ጋር ባደረገችው ትብብር ግብፆች ተቆጥተዋል። ስለሆነም ሱዳንን ለማናደድ ሱዳን ሳትኖር ከኢትዮጵያ ጋር በአባይ ጉዳይ ላይ እንደራደር የሚል ጥያቄ አቅርበዋል። ከኢትዮጵያ አይቻልም የሚል ምላሽ በማግኘታቸው ኤርትራ ጦራቸውን በማስገባት የኤርትራ ወታደሮችና የኢትዮጵያን ተቃዋሚዎችን በማሰልጠንና በማስታጠቅ ኢትዮጵያን የማተራመስ ሥራ ይሠራሉ የሚሉት አቶ ካህሳይ ናቸው።

ፕሮፌሰር መረሳ ደግሞ፤ የኤርትራና የግብፅን የማተራመስ ስልት ለመቀልበስ መንግሥት የተመጣጣኝ እርምጃውን አካሄድ ማየትና ካለው ነባራዊ ሁኔታ ጋር የሚሄድ ስልት መከተል አለበት ባይ ናቸው። የኤርትራ መንግሥት በአረብ አገራት ቁጥጥር ስር ነው። ግብፅ በኤርትራ ስልታዊ ቦታ እየያዘች ናት። ወደ ታላቁ የህዳሴ ግድብም እየቀረበች ነው። ሌላም ሌላም ሸፍጦችን እየሠራች ትገኛለች። ይህ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅም ላይ አደጋ የሚጋርጥ ነው ሲሉም ያስጠነቅቃሉ።

«በኢትዮጵያ ላይ የተነሱ ጦርነቶች ሁሉ መነሻቸው በኤርትራ በኩል ነው። በመሆኑም በኤርትራና በቀይ ባህር ላይ ያለንን ፖሊሲ እንደገና ማስተካከል አለብን። የኤርትራ ጉዳይ የውጭ ጉዳይ ሳይሆን የውስጥ ጉዳይ አካል አድርጎ ማየትና የግብፆችና የሌሎች አገራት መስፋፋት በጥንቃቄ መጠበቅ ያስፈልጋል። ከአረብ አገራት ጋር ያለንን ግንኙነት እንደገና ማየትና መከለስ ይኖርብናል።

ከሱዳን ጋር ያለንን ትብብር ማጠናከር፤ ከታችኞቹ የአባይ ተፋሰሰ አገራት ጋር ያለውን ግንኙነትም ማሳደግ ይገባል። የአገር ውስጥ ችግሮቻችንንም መፍታት፥ እራስንም ለሁሉም ነገር ዝግጁ ማድረግ ይገባል›› ሲሉ ይመክራሉ።

አቶ ካህሳይ በበኩላቸው፤ በኢትዮጵያና በሱዳን መካከል ያለውን የጋራ ጥቅም በማሰብ ግንኘነቱን ማጠናከር፥ የግብፅና የኤርትራ ግንኙነትን በዓይነ ቁራኛ መከታተል፥ በሱዳን ውስጥ ፖለቲካዊ መረጋጋት እንዲኖር ማገዝ፥ ከአረብ አገራት ጋር ያለውን ግንኙት በሱዳን በኩል ማጠናከር አስፈላጊ መሆኑን ያነሳሉ።

«የውጭ ጥንካሬያችን የውስጥ ጥንካሬያችን በመሆኑ ውስጣዊ አንድነታችንን ማጠናከር በውስጥ ያሉብንን ችግሮች መፍታት፤ የመከላከያ አቅማችንን አቅም ማደራጀት፥ ከሱዳን በተጨማሪ በቅርብት ያሉ ጎረቤቶቻችንን በጥንቃቄ መያዝና ግንኙነቱን እያጠናከሩ መሄድ፥ በቀይ ባህር አካባቢ የራሳችንን ጥቅም ለማስከበር መሥራት፥ ከሱዳን ጋር ያለውን ግንኙት ወደ ቀጥተኛ ትግበራ በማሸጋገር ጥቃት ከተሰነዘረ በጋራ እስከመመከት የሚደርስ እርምጃ ለመውሰድ መዘጋጀት፥ አገራችንን መጠበቅ የሚያስችልና ከወቅቱ ንባራዊ ሁኔታ ጋር የሚሄድ መከላከያ መገንባትም የሚያስችል ዝግጅት ማድረግ ይገባል» የሚሉት ደግሞ አቶ ልደቱ አያሌው ናቸው።

ግብፅ በምሥራቅ አፍሪካ ያላትን ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጥቅም ለማስከበር ከዚህ ቀደም የደቡብ ሱዳን ተቃዋሚዎችን ደብድባለች፤ ከኢትዮጵያ ጎረቤት አገራት ጋር ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቷን ለማጠናክር ስትሠራ ቆይታለች። የአሁኑ እንቅስቃሴዋም ከዚያ የቀጠለ መሆኑን ምሁራኑ ይናገራሉ።

ምሁራኑ ግብፅ በኤርትራ ጦሯን ማስገቧቷ በኢትዮጵያና በሱዳን ላይ በቀጥታና በተዘዋወሪ ጉዳት ማድረሱ አይቀርም ይላሉ። በተለይም ኤርትራ በማትቆጣጠራቸው የአገሪቷ በረሃማ አካባቢዎች ሽብርተኞች መፈልፈላቸው አይቀርም፤ የኢትዮጵያ ተቃዋሚዎችን በማስታጠቅም አገሪቷን ሊያውኩ ይችላሉ። በመሆኑም ይሄንን እንቅስቃሴ በቅርብ ርቀት በመከታተል አስፈላጊው እርምጃ መውሰድ ይገባል ብለዋል።
ዜና ትንታኔ አጎናፍር ገዛኸኝ (Ethiopian Press Agency.)

No comments:

Post a Comment