Sunday, January 28, 2018

የወቅቱ የአገሪቱ ችግር ሊፈታ የሚችል ነው

(Jan 28, (ኢትዮጵያ ))--አሁን በኢትዮጵያ ያለው ድባብ ከባድ ይመስላል። ይህ የሚከብድ ድባብ የተፈጠረው በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች በተፈጠሩ ለሰው ህይወት መጥፋት ምክንያት በሆኑ ተከታታይ ግጭቶች ሳቢያ ነው። በተለይ ከ2009 ዓ.ም መጀመሪያ አንስቶ ሲካሄድ የቆየው በኦሮሚያና በኢትዮጵያ ሶማሌ አዋሳኝ አካባቢ የተቀሰቀሰ ግጭት ቀዳሚው ምክንያት ነው። ይህ ግጭት በራሱ ለበርካታ ዜጎች ህይወት መጥፋትና በመቶ ሺዎች ለሚቆጠሩ መፈናቀል ምክንያት ከመሆኑ በተጨማሪ ለሌሎች ጥያቄዎችና ችግሮችም መንስኤ ሆኗል።

በተደጋጋሚ ሲነገር እንደቆየው፣ በሁለቱ ክልሎች አዋሳኝ አካባቢዎች ለተፈጠረው አለመግባባትና ግጭት መንስኤ በህዝበ ውሳኔ የተረጋገጠው ወሰን መሬት ላይ ሳይካለል መቆየት ነው። አለመግባባቱንና ግጭቱን የጫረው ይህ የወሰን አለመካለል ነው ቢባልም፣ ግጭቱ ግን አዋሳኝ አካባቢዎች በሚኖሩ የሁለቱ ክልሎች ብሄሮች ጎሳዎች መሃከል የተካሄደ ነው ማለት አይቻልም።

የሁለቱ ክልሎች አዋሳኝ አካባቢዎች ነዋሪዎች እንደሚናገሩት፣ እነርሱም ለግጭቱ ባዳዎች ናቸው። ግድያዎች የሚፈጸሙት የአካባቢው ነዋሪ ባልሆኑ፣ በተደራጁና የውጊያ መሳሪያ በታጠቁ ቡድኖች ነው። ይህ ችግር በየወቅቱ ያለማቋረጥ ለሰዎች ህይወት መጥፋት ምክንያት መሆኑና የፌዴራል መንግስት ይህን በአፋጣኝ አስቁሞ ለችግሩ እልባት ማበጀት አለመቻሉ የችግሩ ሰለባ የሆነው ህዝብ በፌዴራል መንግስቱና በሀገሪቱ ሰላም አስከባሪ ሃይል ላይ ያለው እምነት እንዲሸረሸር አድርጓል።

የግጭቱ መዘዝ በዚህ አላቆመም። በተለይ ከጷግሜን 2009 ዓ.ም ጀምሮ ግጭቱ ተባብሶ በሁለቱም ወገን በመቶ ሺህ ለሚቆጠሩ ሰዎች መፈናቀልና ቁጥራቸው እስካሁን በይፋ ለማይታወቅ ሰዎች ሞት ምክንያት መሆኑ፣ ጉዳዩ ከሁለቱ ክልሎችም አልፎ የቀረውን የኢትዮጵያ ህዝብም ግር አሰኝቷል። መንግስት ይህን ችግር ለዘለቄታው መፍታት፣ መፍታት ባይችል እንኳን ግጭቱን ማስቆም እንዴት ያቅተዋል?! የሚል ቁጭት ቀመስ ጥያቄ ጭሯል።

በተለይ በኦሮሚያ ውስጥ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ጉዳዩን በጥያቄ መልክ አንስተው ትምህርት ለማቆም እንደምክንያት አቅርበውታል። እውነቱን ለመናገር ይህ ጉዳይ በኦሮሚያ ክልላዊ መንግስትና በፌዴራል መንግስት እንዲሁም በኢህአዴግ ድርጅቶች መካከል የተለመደው ተናቦ የመስራት እንቅስቃሴ እንዲደፈርስ ምክንያት ሆኗል።

ከዚህ በተጨማሪ እዚያም እዚህም የግለሰቦችን ግጭትና መሰል ተልካሻ ምክንያቶች በስውር እጅ ወደ ብሄር ግጭትነት እንዲቀየሩ የተደረገበት ሁኔታም አለ። እነዚህ የየአካባቢው ጥቃቅን ግጭቶች በኦሮሚያና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልሎች መሃከል ከተፈጠረው ሰፋ ያለ ግጭት ጋር ተዳምረው ሀገሪቱን የተተራመሰችና መንግስት ሀገሪቱን መምራት ያቃተው የሚያስመስሉ ሁኔታዎች ፈጥሯል። የሚከብድ ድባብ ያልኩትም ይህንን ነው።

እነዚህ ሁኔታዎች ሳይመች ሰላማዊ የምርጫ ሂደትን፣ አመቺ ሲመስላቸው ደግሞ ሃይልን ጨምሮ ማንኛውንም ወደስልጣን ያደርሳል ብለው ያሰቡትን አቅጣጫ የሚከተሉ የፖለቲካ ፓርቲዎችና በውጭ ሀገር ህገመንግስታዊ ሥርዓቱን ለማፈረስ መልካም አጋጣሚዎችን በመጠባበቅ ላይ የሚገኙ ቡድኖችን ከተኙበት ቀስቅሰዋል።

ሰሞኑን ሰላማዊ የፖለቲካ እንቅስቀሴ ለማድረግ ህጋዊ እውቅና የተሰጣቸው ሰማያዊ ፓርቲና የመላው ኢትዮጵያውያን አንድነት ድርጅት (መኢአድ) በውጭ ሀገር ከሚኖር ወደስልጣን መሹለኪያ ቀዳዳ ያለ ሲመስለው ብቻ ድምጹን ከሚያሰማ የኢትዮጵያ ህዝብ የጋራ ትግል ሸንጎ ከተሰኘ ቡድን ጋር በጋራ ለመስራት መስማማታቸውን ሰምተናል። በጋራ ለመታገል የተስማሙት ጊዜው አመቺ ስለሆነ ከምርጫ ውጭ ወደስልጣን የሚመጡበት እድል የተገኘ መስሏቸው ይህ እንዳያመልጣቸው አስበው ነው። በጋራ ለመታገል መስማማታቸው ምንም ችግር የለውም።

በስልጣን ላይ ያለው መንግስት በሌላ መተካት አለበት በሚል የያዙትም አቋም በራሱ ምንም ችግር የለውም። የስልጣን ሽግግሩ ከምርጫ ውጭ በሆነ መንገድ እንዲከናወን ያስቀመጡት ሃሳብ ግን ጤናማ አይደለም። ሌሎች በሀገር ውስጥ የሚንቀሳቀሱ ፓርቲዎችም እንዲሁ ለምሳሌ መድረክ ከምርጫ ውጭ የስልጣን ሽግግር ይደረግ የሚል አቋሙን ጮክ ብሎ ማሰማት ጀምሯል። በዚህ ጽሁፍ የሰማያዊ ፓርቲ፣ የመኢአድና ራሱን የጋራ ትግል ሸንጎ ብሎ የሚጠራ ሰሞነኛ ቡድን አቋምና አካሄድ ላይ አተኩራለሁ።

ለጋራ ትግል ተሰባሰብን ያሉት እነዚህ ፓርቲዎች ስልጣን ላይ ያለው መንግስት አብቅቶለታል ባዮች ናቸው። በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የተቀሰቀሱ ግጭቶችን ለዚህ አስረጂነት ይጠቅሳሉ። አሁን በስልጣን ላይ ያለው መንግስት የጎሳ ፖለቲካ ስለሚያራምድ ውጤት ማምጣት አይችልም፤ የአንድነት ሃይሎች ተባብረው ድል ሊያመጡ ይችላሉ የሚል አቋም እንዳላቸውም ገልጸዋል። ይህን መንግስትን የመቀየር ፍላጎታቸውን ለማሳካት ለህገመንግስታዊው የምርጫ ሂደት ቦታ አልሰጡትም።

ለጋራ ትግል ውል ገብተናል ካሉት አንዱ የሆነው የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር አቶ የሺ ዋስ አሰፋ በዚህ ጉዳይ ላይ በሰጡት አስተያየት፤ ኢትዮጵያ ውስጥ ለውድድር የሚያበቃ ምርጫ ቦርድ፣ ሚዲያ፣ የፍትህ ሥርዓት የመሳሰሉት ስለሌሉ ወደትግል ገብተናል ብለዋል። ወደስልጣን ለመምጣት የምርጫን አማራጭ እንደማይቀበሉ ያመለከቱት እነዚህ በጋራ እንታገላለን የሚሉ ቡድኖች፣ አሁን ያለውን መንግስት የሚያስወግዱበት መንገድ ላይ ግን ግልጽ አይደሉም። ሁሉም የተካተተበት ውይይት ይደረግ፣ የሽግግር መንግስት ይመስረት፣ ህገመንግስትም የቀረጽ የሚል የተደበላለቀ ነገር ያነሳሉ፡፤

የፖለቲካ ፓርቲዎቹን የጋራ ትግል የሚል ነገር ውስጥ የከተታቸው ከላይ የገለጽነው በተለይ ከ2008 ዓ.ም ጀምሮ ሀገሪቱ ውስጥ የተቀሰቀሰው ተቃውሞ፣ ሁከትና ግጭት ነው። እነዚህ ነባራዊ ሁኔታዎች መንግስት ያበቃለት መሆኑን ያመለክታሉ፤ ስለዚህ ከምርጫ ውጪ ወደ ስልጣን የምንመጣበትን ወይም ትንሽም ቢሆን የምንጋራበትን እድል እንድናገኝ መንግስትን እንግፋው በሚል ስሜት ነው የተነሳሱት። እዚህ ላይ አንድ በግልጽ መታወቅ ያለበት ነገር፣ አቋማቸው መንግስትን ህገመንግስታዊ ባልሆነ መንገድ አስወግደው ስልጣን ላይ የሚወጡበትን ሁኔታ መሞከር ነው።

እርግጥ ነው፤ ኢትዮጵያ ውስጥ ሁከት በተፈጠረ ቁጥር መንግስት ሊፈርስ እየመሰላቸው ካንቀላፉበት እየተነሱ ስለስልጣን ድልድል የሚያወሩ ቡድኖችን ማዳመጥ አዲስ ነገር አይደለም። ከላይ የተጠቀሰው የእነሰማያዊ ፓርቲ ወሬም ከእነዚህ አንዱ ነው። እዚህ ላይ አሁን ስልጣን ላይ ያለውን መንግስት ከምርጫ ውጭ ማስወገድ የግድ የሚል ነባራዊ ሁኔታ አለወይ? እርግጥ መንግስት ሀገሪቱን መምራት አቅቶታል ወይ? የሚሉትን ጥያቄዎች ማንሳት ተገቢ ነው።

በሀገሪቱ ውስጥ ስጋት የፈጠሩ የግጭት ችግሮች መኖራቸው እውነት ነው። መንግስት ለተቀሰቀሱት ግጭቶች ወቅታዊ ፖለቲካዊና ህጋዊ መፍትሄዎች ማበጀትም ላይ ክፍተት ታይቶበት ቆይቷል። መንግስትም እነዚህ ክፍተቶች እንዳሉበት አስታውቋል፡፡

አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ለችግሮቹ ወቅታዊም ይሁን ዘላቂ መፍትሄ ማበጀት የሚችለው በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ነው። በስልጣን ላይ ያለውን መንግስት ከምርጫ ውጭ ከስልጣን ለማስወገድ በማሰብ የሚነዛ ውዥንብር፣ ከውጭ ሃይሎች ጋር በመሆን መንግስት ላይ ጫና ለማሳደር የሚደረግ እንቅስቃሴ ችግሩን በማወሳሰብ መፍትሄ የማበጀቱን እርምጃ ከማደነቃቀፍ የተለየ ምንም የሚያስገኘው ፋይዳ የለም።

ግጭት ውስጥ የገቡት ሁለቱም ብሄራዊ ክልላዊ መንግስታት በኢፌዴሪ ህገመንግስት ላይ የማይናወጥ እምነት ያላቸው መሆኑን መጥቀስ ይገባል። ህገመንግስታዊ ሥርዓቱን የሚገፋ ማንኛውንም እርምጃ አይቀበሉም። ህገመንግስታዊውን ሥርዓት የሚፈታተን የከፋ አደጋ የመጣ ከመሰላቸው ተነጥለው የየራሳቸውን ክልል ማስተዳደር ወደ ሚያስችላቸው እርምጃ ከማምራት የማይመለሱ መሆኑም መታወቅ አለበት። ይህ ደግሞ የሀገሪቱን አንድነት አደጋ ላይ ይጥላል፡፡

በዚህ ሁኔታ እነሰማያዊ ፓርቲ የሚያስቡት መንግስትን ገፍቶ የማስወገድ ህልም ቢሳካ ችግሩ ማንም ሊይዘው የማይችለው ውል አልባ ሆኖ ሀገሪቱን ሊበታትናት ወደሚችልበት ደረጃ መሸጋገሩ አይቀሬ ነው። እነሰማያዊ ፓርቲ ማስታወስ ያለባቸው የሀገሪቱ የመንግስት ስልጣን ያለው አዲስ አበባ ቤተመንግስት ሳይሆን ዘጠኙ ክልላዊ መንግስታት ጋር መሆኑን ነው። በሃይል አራት ኪሎ ቤተ መንግስት ቢገቡ፣ ሊጨብጧቸው የማይችሏቸው ዘጠኝ ትንንሽ መንግስታት እንዲፈጠሩ ከማድረግ ያለፈ የሚያተርፉት ነገር የለም።

እርግጥ አሁን በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ችግሮቹን እንዳይፈታ ያደረጉትን ድክመቶቹን በይፋ ለህዝብ አሳውቆ፣ ችግሩን በተጨባጭ ሊፈታ የሚችል መፍትሄ በማቅረብ ከሁለት ዓመት ተኩል በኋላ በሚካሄደው ሀገራዊ ምርጫ ላይ በመወዳደር በዘጠኙም ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ለስልጣን የሚያበቃ ውክልና በማግኘት ወደስልጣን መምጣት ይቻላል። እነሰማያዊ ፓርቲ ግን ይህን አማራጭ ይፈሩታል።

በመሰረቱ ሰማያዊ ፓርቲና አጋሮቹ ነን ባዮቹ አሁን በያዙት አቋም በሀገሪቱ ያጋጠሙ ችግሮችን መፍታት አይችሉም። ኢትዮጵያ ውስጥ የየራሳቸው ማንነት ያላቸው ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች የመኖራቸውን ግዙፍ እውነታ እንኳን መቀበል የማይፈልጉ ብሄሮችን ጎሳ በሚል ፍረጃ እንደ ተራ ነገር የሚያንቋሸሹ ሰማያዊ ፓርቲን የመሳሰሉ ቡድኖች አሁን ያለው የሀገሪቱ ነባራዊ ሁኔታ የፈጠራቸው አይደሉም። እነዚህ ቡድኖች የባለፉት አሃዳዊ ሥርዓቶች ቅሪቶች ናቸው።

 አንድ ሥርዓት ሲወገድ አመለካከቱ በቀላሉ ብን ብሎ አይጠፋም። በመቶ ለሚቆጠሩ ዓመታት የሚኖርበት ሁኔታ አለ። በአሜሪካ የባሪያ አሰዳሪ ሥርዓት ካከተመ ሁለት ክፍለ ዘመን ያስቆጠረ ቢሆንም አሁንም የባሪያ አሳዳሪ አመለካከትን የሚያራምዱ ቡድኖች መኖራቸውን ልብ ማለቱ ጥሩ ነው። ሰማያዊ ፓርቲና መሰሎቹ የዚህ አይነት ያረጀ አመለካከት ቅሪቶች ናቸው።

ያከተመላቸው ሥርዓቶች ቅሪት አመለካከቶች ህልውናቸው ሙልጭ ብሎ ባይጠፋም፣ የበላይ ሆኖ የመውጣት ምንም እድል የላቸውም። በአሜሪካ የባሪያ አሳዳሪ ሥርዓት በምንም ምድራዊ ሁኔታ ሊመለስ አይችልም። መቼም ቢሆን ገዢ አመለካከት ሊሆን አይችልም። በሌላ አነጋገር ገዢ ፓርቲ የመሆን እድል ከቶም የለውም። እርግጥ ምክር ቤት ውስጥ በአንድ በሁለት መቀመጫዎች ውር ውር የሚልበት እድል ሊኖር ይችላል።

በኢትዮጵያ ሁኔታም ያለፉት ሥርዓቶች ቅሪት አመለካከቶች እጣ ፈንታ ከዚህ የተለየ አይደለም። አንድ ሁለት የምክር ቤት መቀመጫ ሊያገኙ የሚችሉበት እድል ሊኖር መቻሉ ግን አይካድም። በተለይ የፖለቲካ ፓርቲዎች ባደረጉት ድርድር እንዲስተካከል ሃሳብ ያቀረቡበት የአብላጫና ተመጣጣኝ ቅይጥ የምርጫ ሥርዓት ህጋዊ ሆኖ ስራ ላይ ከዋለ የቀደሙት የአሃዳዊ ሥርዓት አመለካከት አራማጆች አንድ ሁለት መቀመጫ ሊያገኙ የሚችልበት እድል ይኖራል። ከዚህ ግን አያልፉም።

እናም ሰማያዊ ፓርቲና አጋሮቹ አሁን በስልጣን ላይ ያለው መንግስት አብቅቶለታል ወይም ሀገሪቱን መምራት አልቻለም የሚለው አቋማቸው ትክክል እንኳን ቢሆን አሁን የተፈጠረው ችግር የመፍትሄ አካል እንኳን የመሆን ብቃት የላቸውም። የመንግስት ለውጥ፣ የሽግግር መንግስት፣ ህገመንግስት መቅረጽ ምንትስ ቅብጥርስ የሚለው ወሬያቸው የዋሆችን ከማደናገርና ምናልባት በውጭ ሀገር ከሚኖሩ የአሃዳዊ ሥርዓት ተስፈኛ ርዝራዦችን ቀልብ በመማረክ ዶላር መሰብሰብ ያስችላቸው እንደሆን እንጂ በተጨባጭ የሚያበረክተው ምንም አስተዋጽኦ የለውም።

በሌላ በኩል፣ በሀገሪቱ ችግሮች መኖራቸው ባይካድም አሁን በስልጣን ላይ ያለው መንግስት ሀገሪቱን መምራት ያቃተው ደረጃ ላይ አልደረሰም። እዚህም እዚያም ግጭቶች ቢኖሩም በሀገሪቱ አሁንም ህግና ሥርዓት የበላይነት አለው። በሀገሪቱ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እንቅስቃሴዎች እንዲሁም የውጭ ግንኙነትና ዓለም አቀፍ ተሳትፎ በነበረበት ሁኔታ ቀጥለዋል። የቱሪስት ፍሰቱ፣ የውጭና የሀገር ውስጥ ኢንቨስትመንት በታቀደለት መሰረት እየተጓዘ ነው። የተጀመሩ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች የህዳሴውን ግድብ ጨምሮ ያለምንም መስተጓጎል እየተከናወኑ ናቸው። የሀገሪቱ አጠቃላይ የኢኮኖሚ እድገትም እንደቀጠለ ነው።

አሁን ያለው ችግር በዚህ ዋና የሀገሪቱ መገለጫ ውስጥ አንድ ቦታ ላይ እንዳጋጠመ ቁስል የሚወሰድ ነው። የቆሰለ ሁሉ አይሞትም። እናም መንግስት ሀገሪቱን መምራት አላቃተውም፣ አላለቀለትም። ልዩ ትኩረት የሚጠይቁ ችግሮች ግን ገጥመውታል። እነዚህን ችግሮች ከህዝብ ጋር በመሆን የመፍታት እድል አለው። ይህን ማድረግ ካልቻለ ደግሞ ብቸኛ የመንግስት ሥልጣን ምንጭና ባለቤት የሆነው ህዝብ በምርጫ ውክልናውን ነፍጎ ከስልጣን ያነሳዋል፤ በቃ። እውነታው ይሄው ነው።
ኢብሳ ነመራ (ኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት)

No comments:

Post a Comment