Saturday, December 09, 2017

ሲሾም ያልሠራ ሲሻር ሊቆጨው ይገባል!

(Dec 09, (ርዕሰ አንቀፅ))--‹‹ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል›› ይሉትን ኋላቀርና ኪራይ ሰብሳቢነትን የሚያበረታታ አባባል ይዘን ዘመናትን ተሻግረናል፡፡ ኋላቀርና ጊዜው ያለፈበት ኪራይ ሰብሳቢነትን የሚያበረታታ አስተሳሰብ መሆኑን እየተረዳንም ጭምር ዛሬም ድረስ አብሮን እንዲዘልቅ ፈቅደንለታል፡፡ ለዚህም ነው ህዝብን ያገለግላሉ፤ ሀገርን ያሳድጋሉ ብለን ተስፋ የጣልንባቸው ሹመኞች ሕዝብና መንግሥት የሰጣቸውን ስልጣን ወደጎን በመተው ለግል ፍላጎታቸው ማስፈጸሚያ ሲያደርጉት የሚታዩት፡፡

የሰው ልጅ በህይወት ዘመኑ ሊኮራባቸው ከሚገቡት የሕይወት ጉዞው መካከል የማያስቆጩና ለትውልድ የሚተላለፉ መልካም ሥራዎችን ሠርቶ ማለፍ ተቀዳሚው ተግባር ነው፡፡ ያ መልካም ሥራ ደግሞ የሚለካው በተሰማራባቸው ትንሽም ይሁን ትልቅ የሥራ መስኮች ታማኝ ሆኖ ማህበረሰቡን በሚጠቅም ሥራ ላይ በመሰማራቱ ነው፡፡

ለሥራው ታማኝ ሆኖ ለመገኘት ደግሞ ለሥራው የሚስማማ ህሊናዊ የሥነምግባር መመሪያ ሊኖረው ይገባል፡፡ ቀጥሎም ራሱ ላበጃቸው ክቡር የህሊና መመሪያዎች ታማኝ መሆን ይጠበቅበታል፡፡ ያኔ በተረታ ተረቶችም ሆነ በሌሎች ጎታች አስተሳሰቦች ሊጠለፍ አይችልም፡፡ ምክንያቱም የርሱ የህይወት ፍልስፍና ሙያውን ማክበር፣ ሌሎችን ማገልገልና የተሰጠውን የኃላፊነት ቦታ ለተሰጠው ዓላማ ማዋል ብቻ ይሆናል፡፡

መንግሥት በጥልቅ ተሃድሶ በአካሄደው ግምገማ የለያቸው መሰረታዊ ችግሮች ለመንግሥት ስልጣን የ አተያይ መዛባት፣ ከፖለቲካዊና ርዕዮተ-ዓለማዊ ዝግጁነት ጉድለት፣ ከመልካም አስተዳደር ጉድለቶች፣ ከፀረ-ዴሞክራሲና አድርባይነት፣ ከኪራይ ሰብሳቢነትና ከህዝቡ ከፍተኛ የመልማት ፍላጐት የመነጩትን አዳዲስ ፍላጎቶች ፈጥኖ ማሟላት አለመቻል ናቸው።

በጥልቅ ተሃድሶው የተለዩ ችግሮችን ለመፍታት በተደረገው ጥረት የአመራር አደረጃጀት ላይ ዓይነተኛ ለውጥ ተደርጓል፡፡ የህዝቡን ተደማሪ ጥያቄና ፍላጐቶች በተሻለ አስተሳሰብ ለመመለስ የሚያስችሉ ተከታታይ ሥራዎችም በመከናወን ላይ ናቸው፡፡ በጥልቀት የመታደስ ንቅናቄው በፈጠረው አዲስ የመነቃቃት መንፈስም ኃላፊነታቸውን አለአግባብ በሚጠቀሙና ህዝቡን በማገልገል መርካት በማይሹ አመራሮችና ባለሙያዎች ላይ የማስተካከያ ፖለቲካዊ፣ ህጋዊና አስተዳደራዊ ዕርምጃ መውሰድ ተጀምሯል፡፡ ይህም አሁንም በየደረጃው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ይጠበቃል።

ጥልቅ ተሃድሶው ወዲህ ኢኮኖሚያዊ ዕድገቱን ከማስቀጠሉ በተጨማሪ መልካም አስተዳደር በማስፈን ሂደትና በፀረ-ሙስና ትግሉ ዙሪያ፣ ህዝቡን በስፋት ለማሳተፍና የትግሉ ቀጥተኛ ባለቤት እንዲሆን በማድረግ ረገድ እየተደረጉ ያሉት ጥረቶችና የተገኙት ለውጦች ተስፋ ሠጭዎች ናቸው፡፡

አሁን በአመራሩ የሚታየው ጥንካሬ እንደተጠበቀ ሆኖ በትግልና በፍጥነት ሊታረሙ የሚገባቸው በርካታ ችግሮች አሁንም አልተወገዱም፡፡ ህዝቡን ከፊት ሆኖ በመርህ ከመምራት ይልቅ ስልጣንን ለግል ፍላጎት ማስፈጸሚ አድርጎ ማየት ይታያል፡፡ በዚህ ሳቢያ በተለያዩ አካባቢዎችና አጋጣሚዎች እየተከሰቱ ያሉ ግጭቶችና ልዩነቶችን አመራሩ የሚይዝበት መንገድ ወጥነት መጓደል የመነጩ መሆናቸውን መረዳት ይገባል፡፡

በመንግሥት ሠራተኛው ውስጥ በተካሄዱ የጥልቅ ተሃድሶ መድረኮች ሠራተኛው የአገልጋይነት መንፈስ ማነስና ውጤታማ አገልግሎት አለመስጠት ዋንኞቹ ችግሮች ነበሩ፡፡ ችግሮቹን ለመፍታት የሚያስችሉ ጥረቶች ቢደረጉም አሁንም በሚፈለገው ደረጃ የህዝብን እርካታ ለማረጋገጥ ባለመቻሉ ቀጣይ ትግል የሚጠይቅ ሆኗል፡፡

በተዛባ የስልጣን አተያይ ምክንያት ሀገሪቷ ካመነጨችው ምጣኔ ሀብት ተጠቃሚ መሆን የጀመረውን ህዝብ የሚያስከፉ የመልካም አስተዳደር ችግሮች አሁንም እየተስተዋሉ ነው፡፡ አንገብጋቢ ከነበሩት የመልካም አስተዳደር ችግሮች መካከል፤ በገጠርና በከተማ ለሚገኙ ወጣቶች የሥራ ዕድል ፈጠራ ደካማ መሆኑ ይጠቀሳል፡፡ በመሆኑም ሥራ ፈላጊዎችን የመለየት፣ የማደራጀት፣ የማሰልጠን ሥራዎች ተከናውነዋል፡፡

በዚህም አበረታች ውጤቶች ተመዝግበዋል፡፡ ይሁን እንጅ አሁንም በርካታ ሥራ አጦች የሚመለከታቸው አካላት ጥያቄያቸውን እየፈቱላቸው አለመሆኑን በምሬት በመናገር ላይ ናቸው፡፡ መንግሥት የፈቀደላቸውን ተዘዋዋሪ የብድር ፈንድ እንዳያገኙ የዞንና የወረዳ አመራሮች እንቅፋት እንደሆኑባቸውም ደጋግመው ሲናገሩ ይደመጣል፡፡

ህዝቡን እንዲያገለግሉ ኃላፊነት የተሰጣቸው መንግሥታዊ ተቋማት ዛሬም የእሮሮ ምንጭ እንደሆኑ ቀጥለዋል፡፡ ውሃ፣ መብራትና ሌሎች አገልግሎቶች በአግባቡ ለህብረተሰቡ እየደረሱ አይደሉም፡፡ መንግሥት በከፍተኛ ድጎማ ለህብረተሰቡ እንዲደርሱ የሚያስገባቸው መሰረታዊ የፍጆታ ዕቃዎች በአግባቡ ለሚመለከታቸው ተጠቃሚዎች ሳይደርሱ የኪራይ ሰብሳቢዎች መጠቀሚያ እየሆኑ ነው፡፡

ህብረተሰቡን ከህገወጥ ነጋዴዎች ጫና ያቃልላሉ ተብለው የተቋቋሙት የሸማቾች ህብረት ሥራ ማህበራት አሁንም የቅሬታ ምንጭ ከመሆን አልወጡም፡፡ የህክምና ተቋማት ከተደራሽነታቸው ማነስ በተጨማሪ በአገልግሎት አሰጣጣቸው ዛሬም የህብረሰቡን ፍላጎት እያረኩ አይደሉም፡፡

የትራንስፖርት አቅርቦቱን ለማሻሻል በርካታ ጥረቶች ቢደረጉም በአደረጃጀትና በአሠራር መጓደል አሁንም ተገልጋዩን ማርካት አልተቻለም፡፡ በከፍተኛ ደረጃ እያደገ ለመጣው የመኖሪያ ቤት ጥያቄ በቂ ምላሽ መስጠት አልተቻለም፡፡

እነዚህና ሌሎች በርካታ ችግሮች ሊፈቱ ያለመቻላቸው ምስጢር ከኢኮኖሚው አቅም ጋር ተያይዞ ያለው ማነቆ እንደተጠበቀ ሆኖ ያለውን ውስን ሀብት በተገቢው መንገድ ጥቅም ላይ ያለማዋሉ ችግር መንስኤ አሁንም ለስልጣን ያለው የተዛባ አተያይ መሆኑ አይካድም፡፡ ሁሉም በየደረጃው ባለው ኃላፊነት የሚጠበቅበትን ባለመሥራቱ ካለቆጨው አሁንም ከኋላቀሩ አስተሳሰብ አለመውጣቱን አመላካች ነው፡፡

በመሆኑም ከላይ የተጠቃቀሱትን የቅሬታ ምንጮችን ለማድረቅ የተጀመረው መልካም አስተዳደርን የማስፈን ተግባር በመቆጨት መንፈስ የሚከናወን ዋነኛ የርብርብ ማዕከል ሆኖ ሊቀጥል ይገባል፡፡ ሲሾም ያልሠራም ሲሻር ሊቆጨው ይገባል። ሃገርና ህዝብ መጥቀም በሚችልበት ቦታ ሆኖ መጥቀም ሳይችል ቀርቷልና።
ኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት

No comments:

Post a Comment