Wednesday, October 12, 2016

አዋጁ የህዝቡን ሰላምና ደህንነት ከማረጋገጥ የተለየ ዓላማ እንደሌለው መንግስት ገለጸ

(ጥቅምት 2፣ 2009, (አዲስ አበባ))--የሚኒስትሮች ምክር ቤት ያወጀው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የህዝቡን ሰላምና ደህንነት ከማረጋገጥ የተለየ ዓላማ እንደሌለው የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ገለጸ።

ካለፈው ቅዳሜ ጀምሮ ተግባራዊ በሆነው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅና በሀገሪቱ ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ተቀማጭነታቸውን በአዲስ አበባ ላደረጉ የመካከለኛው ምስራቅ፣ የእስያና አሜሪካ ሀገራት አምባሳደሮችና ዲፕሎማቶች ገለፃ ተደርጓል፡፡ ለዲፕሎማቶቹ ገለፃ ያደረጉት የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሚንስትር አቶ ጌታቸው ረዳ እንደተናገሩት አዋጁ የዜጎችን መብት አይገድብም፡፡

ኃላፊ ሚንስትሩ ለዲፕሎማቲክ ማህበረሰቡ እንደገለፁት ባለፉት ጥቂት ወራት የህዝቡን ሰላምና ደህንነት አደጋ ላይ የጣሉ፣ መሰረተ ልማቶችን ያፈረሱና ህይወት የቀጠፉ አደጋዎች ተፈጽመዋል፡፡ በሀይማኖቶችና በብሔረሰቦች መካከል ግጭትን የሚቀሰቅሱ ተግባራትም ሲከናወኑ ቆይተዋል ብለዋል፡፡ ይሁንና ህዝቡ ባነሳቸው ህጋዊ ጥያቄዎች ሽፋን የተፈፀሙትን ተግባራት በመደበኛ የህግ ማስከበር ስርዓት ማስቆም ባለመቻሉ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መታወጁን ገልፀዋል፡፡

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የዜጎችን መብቶች የገደበ አለመሆኑንና የፀጥታ ሀይሉም በጠቅላይ ሚንስትሩ ስር በኮማንድ ፖስት እንዲመራ መደረጉን ሚንስትሩ ጠቅሰው፤ በቀጣይ የፀጥታ ስጋትን በማስወገድ የህብረተሰቡን ጥያቄ እንደሚመለስም አረጋግጠዋል፡፡ አዋጁ ህዝቡ በሕጋዊ መንገድ የሚያነሳቸውን ጥያቄዎች ምላሽ እንዲያገኙ ሁኔታዎችን የሚያመቻች እንጂ አፋኝና ገዳቢ እንዳልሆነም አክለው ጠቁመዋል፡፡

የውጭ ጉዳይ ሚንስትር ዴኤታ አምባሳደር ታዬ አጽቀስላሴ በበኩላቸው በተለያዩ ጊዜያት የተነሱት ተቃውሞዎች የሀገሪቱን የመቻቻል ባህል የሚያጠፉ፣ ደህንነትን የሚጎዱና ሉአላዊነትን አደጋ ላይ የሚጥሉ እንደነበሩ ጠቅሰዋል፡፡ ብጥብጡን በገንዘብና በቁሳቁስ የሚደግፉ የውጭ ሀይሎች እንደነበሩ የሚያሳዩ ተጨባጭ ማስረጃዎች መኖራቸውን ለዲፕሎማቲክ ማህበረሰቡ ገልፀዋል፡፡

አምባሳደር ታዬ አዋጁ በምንም ሁኔታ የሰብዓዊ መብቶች፣ የቪዬና የዲፕሎማቶች መብቶች እና አለም አቀፍ ስምምነቶችንና ህግጋት ላይ ገደብ እንደማይጥል አረጋግጠዋል፡፡ ምንም እንኳ አዋጁ የሰዓት እላፊ ለመደንገግ መብት ቢሰጥም በዚህ ወቅት ምንም ዓይነት ገደብ አልተጣለም ብለዋል ሚንስትር ዴኤታው፡፡
ምንጭ: ከኢብኮ

No comments:

Post a Comment