Saturday, September 26, 2015

የግብፅ ቤተክርስቲያን ኢትዮጵያ ለዕድገቷ የምታከናውናቸውን ተግባራት ትደግፋለች

(መስከረም 15/2008, (አዲስ አበባ))--የግብፅ ቤተክርስቲያን ኢትዮጵያ የህዳሴውን ግድብ ጨምሮ ለዕድገቷ የምታከናውናቸውን ተግባራት እንደምትደግፍ ሊቀ ጳጳስ አባ ታዎድሮስ 2ኛ ገለፁ። ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ታዎድሮስ ዳግማዊ የአሌክሳንድሪያ ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ማርቆስ መንበረ ፓትሪያሊክ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን በመስቀል ደመራ በዓል ላይ እንዲገኙ በተደረገላቸው ግብዣ ወደ ኢትዮጵያ መጥተዋል።


ዛሬ በአዲስ አበባ ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተገኝተውም ቡራኬ ሰጥተዋል። ብፁዕነታቸው በዚሁ ወቅት ነው ኢትዮጵያ ለዕድገቷ የምታከናውናቸውን ተግባራት የግብፅ ቤተክርስቲያን እንደምትደግፍ የተናገሩት። ቤተክርስትያኗ ድጋፍ ከምታደርግባቸው መካከልም ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ በዋነኝነት እንደሚጠቀስ ገልጸዋል።

"አንድ ከሚያደርጉንና ከሚያስተሳስሩን ጉዳዮች ዋናው ነገር የዓባይ ወንዝ ነው" ያሉት አቡነ ታዎድሮስ "የአገራቱ መሪዎችም ምንም ዓይነት ልዩነትና ፀብ እንደማይፈጥሩ እርግጠኞች ነን" ብለዋል።  "የዓባይ ወንዝ እግዚአብሔር በነፃ የሰጠን ስጦታ ነው፣ ሁሉም የሰው ልጆች ከፀሐይና ከነፋስ በነፃ እንደሚጠቀሙ ሁሉ ከዚህም ወንዝ በነፃ ይጠቀማሉ ይህንንም ስጦታ በነፃ እየተጠቀምን በፀጋ እንኖራለን" ሲሉ ነው የተናገሩት።

በአፄ ቴዎድሮስ ዘመነ መንግሥት የተጀመረው የግብፅ ጳጳስት የኢትዮጵያ ጉብኝት አቡነ ታዎድሮስን አምስተኛው ጉብኚ ያደርጋቸዋል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፓትሪያርክ ብጹዕ አቡነ ማትያስ በበኩላቸው አገራቱ ባህልን፣ ቋንቋን፣ሥነ ጽሑፍን፣ ንግድን፣ መንፈሳዊና ማሕበራዊ ጉዳዩችን ያካተተ የቆየ ግንኙነት እንዳላቸው ጠቅሰዋል።

"ከዚህም ባለፈ የአባይ ወንዝን በጋራ የምንጠጣ ታሪካዊያን ሕዝቦች ነን" ሲሉ ተደምጠዋል አቡነ ማትያስ። ወንዙን በአግባቡና በፍትኃዊነት ከተጠቀምንበት ለሌሎች አገራት ጭምር የሚበቃ ማለቂያ የሌለው የአምላክ በረከት መሆኑን በመጠቆም።

ይህን ወንዝ በሠላማዊ መንገድ በመጠቀም የሁለቱ አገራት መንፈሳዊና ማኅበራዊ ግንኙነቶች ለዓለም ምሣሌ በሚሆን መልኩ ተጠናክሮ መቀጠል እንደሚገባው አባታዊ ምክራቸውን አስተላልፈዋል።  የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስና የግብፅ ኮፒቲክ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያናት መንፈሳዊ ግንኙት ከ1 ሺህ 500 ዓመታት በላይ ያስቆጠረ መሆኑን የታሪክ ድርሳት ያስረዳሉ።

በኢትዮጵያ የመጀመሪያው ሊቀ ጳጳስ ሆነው የተሾሙት አባ ሰላማ ከሳቴብርሃን ናቸው።ባለፈው ጥር 2007 ዓ.ም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፓትሪያርክ ከቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ጋር በመሆን በግብጽ ይፋዊ ጉብኝት ማድረጋቸው ይታወሳል።
ምንጭ: የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት

No comments:

Post a Comment