Thursday, September 17, 2015

የግብጽ ቤተክርስቲያን ፓትሪያርክ ኢትዮጵያን ሊጎበኙ ነው

(መስከረም 4/2008, (አዲስ አበባ))--የግብጽ ኮፕቲክ ቤተክርስቲያን ያላትን ተሰሚነት በመጠቀም በአባይ ዙሪያ የሚካሄደው ውይይት ሰላማዊ እንዲሆን የበኩሏን አስተዋጽኦ እንደምታበረክት ገለጸች። ብጹዕ ወቅዱስ አባ ቶዎድሮስ 2ኛ ፓትሪያርክ ዘእስክንድሪያ ወርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘ መንበረ ማርቆስ ከመስከረም 14 እስከ 20 በኢትዮጵያ የሚያደርጉትን ጉብኝት አስመልክቶ በግብጽ ኤምባሲ ጋዜጣዊ መግለጫ ተሰጥቷል።

በመግለጫው ላይ በኢትዮጵያ የግብጽ ቤተክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ አባ በመን እንደተናገሩት የሁለቱም አገራት አብያተ ክርስቲያናት ውይይቱ መልካም ውጤት እንዲያመጣና ሰላማዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ የማድረግ አቅም አላቸው።

በመሆኑም የግብጽ ቤተክርስቲያን አዎንታዊ ሚናዋን ለመጫወት ዝግጁ ነች ብለዋል። የአባይ ወንዝ አገራቱን ከሚያስተሳስራቸው በርካታ ጉዳዮች አንዱ መሆኑን የተናገሩት አባ በመን ይህን የፈጣሪ ስጦታ አገራቱ በአግባቡና ሰላማዊ በሆነ መልኩ ሊጠቀሙበት እንደሚገባ አሳሰበዋል።

ለዚህም አብያተ ክርስቲያናቱ ያላቸውን አቅም በመጠቀም ለሰላማዊነቱ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ሊያበረክቱ ይገባል ነው ያሉት። ቤተክርስቲያኗ በአሁኑ ወቅት አለምን እያስጨነቀ ያለው ሽብርተኝነትና ጽንፈኝነትን ለማስወገድ ሰላምና ፍቅርን በመስበክ እንዲሁም የጽድቅን ስራ በማስተማር እንደምትዋጋውም አስረድተዋል።

ሽብርተኝነት የየትኛውም ኃይማኖት አስተምሮ አይደለም ያሉት አባ በመን ሁሉም እምነቶች በጋራ ሊዋጉት እንደሚገባም አሳስበዋል። የፓትርያርኩ ጉብኝትም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ እና በግብጽ ኮፕቲክ ቤተክርስቲያኖች መካከል ያለውን የረጅም ዘመን ግንኙነት አጠናክሮ ለማስቀጠልና በጋራ ጉዳዮች ላይ ያለውን ትብብር ለማጠናከር ያለመ ነው ብለዋል።

በአብያተ ክርስቲያናቱ መካከል ልምዶችን የመለዋወጥና ተቀራረቦ የመስራቱ ሁኔታ ወደፊትም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አባ በመን ተናግረዋል። የፓትርያርኩ ጉብኝት የእርስ በእርስ ግንኙነቱን ማጠናከርና በኢትዮጵያ የሚገኙ ኃይማኖታዊ የቅርስ ቦታዎችን በመጎብኘት በረከትን ለማግኘት ያለመ ነው ብለዋል።

ፓትርያርኩ መንፈሳዊ ጉብኝት እንደሚያደርጉ፣ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን አባቶች እንደሚቀበሏቸውና በቆይታቸውም ከቤተክርስቲያኒቱ አባቶች ጋር ውይይት እንደሚያካሂዱ አስረድተዋል። ከተለያዩ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት ጋርም ይገናኛሉ ነው ያሉት።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፓትሪያርክ ብጹእ አቡነ ማትያስም ባለፈው አመት በግብጽ ጉብኝት ማድረጋቸው ይታወሳል።
ምንጭ: የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት

No comments:

Post a Comment