Monday, April 20, 2015

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሊቢያ በሚኖሩ ንጹሐን ወገኖች ላይ የተፈጸመውን ግድያ በጽኑ አወገዘች

(አዲስ አበባ ሚያዚያ 12/2007))--አይ ኤስ የተሰኘው ዓለም አቀፍ አሸባሪ ቡድን በሊቢያ በሚኖሩ ንጹሃን ወገኖች ላይ ''ፈጽሜዋለሁ' በሚል በቪዲዮ ያሰራጨውን ዘግናኝ የግድያ ተግባር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በጽኑ አወገዘች።

የቤተ ክርስቲያኒቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ግድያውን አስመልክቶ ዛሬ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል። የቤተክርስቲያኗ ፓትርያርክ ብጹዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ እንደተናገሩት ቤተክርስቲያኗ ቡድኑ ግፍ በተሞላበት ሁኔታ ያደረሰውን ክፉኛ ታወግዛለች።

''ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በፈጣሪ የተሰጠች ማንኛውም የሰው ልጅ ሕይወት ኃላፊነት በማይሰማቸውና በእነሱ ላይ ሊደረግ በማይፈቅዱ እንዲሁም ምንም ዓይነት ሰብዓዊ ርኀራኄ በሌላቸው እንድትቀጠፍ ስለማተፈቅድ ይህንን አሰቃቂ ድርጊት በጽኑ ታወግዛለች'' ብለዋል።

በንጹሐን ወገኖች ላይ የደረሰው አሰቃቂ ግድያ በመላው ዓለም ባሉ በመገናኛ ብዙኃን እየተሰራጨ መሆኑን አውስተው፣ የግፍ ወንጀል ሰለባዎች ደግሞ ኢትዮጵያውያንና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አማኞች መሆናቸው  አሳዛኝ እንደሚያደርገው ገልጸዋል።

ቤተ ክርስቲያኒቱ የግፍ ሰለባ የሆኑትን ወገኖች ማንነት ተረድታ በሃይማኖታዊና ቀኖናዊ ትውፊት መሰረት አስፈላጊውን ሁሉ እንደምታደርግም ፓትርያርኩ አስታውቀዋል።ሕዝበ ክርስቲያኑና መላው ኢትዮጵያውያንም ሁኔታውን በትዕግሥት እንዲጠብቁ ጠይቀዋል።

ማንኛውንም የሃይማኖት ተቋምና እምነት የማይወክል የአሸባሪዎች ተግባር ሊወገዝ  እንደሚገባው የተናገሩት አቡነ ማትያስ፣የድርጊቱ ፈጻሚዎች ኪሳራ እንጂ ምንም ዓይነት ትርፍ እንደማያገኙ በተግባር ማሳየት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። መንግሥት በውጭ የሚኖሩትን ወገኖች ወደ አገራቸው ለመመለስ  እያደረገ ያለውን ጥረት ቤተክርስቲያኒቷ እንደምትደግፍም አረጋግጠዋል።

ዜጎች ለህይወታቸው፣ለሃይማኖታቸውና ለንብረታቸው ዋስትና ወደ ሌለበት አገር ከመሄድ ይልቅ በአገራቸው ሰርተው ለመለወጥ ቢሞክሩ ቤተ ክርስቲያኒቷ ከሳዑዲ ዓረቢያ ተመላሾች ለሆኑ ዜጎች ያደረገችውን ድጋፍ  ለማድረግ መዘጋጀቷንም ፓትርያርኩ ገልጸዋል።
ምንጭ:ኢዜአ

No comments:

Post a Comment