Monday, April 20, 2015

መንግስት በግፍ ለተገደሉ ዜጎች የሀዘን ቀን ሊያውጅ ነው

(አዲስ አበባ ሚያዚያ 12/2007))--በአይ ኤስ የሽብር ቡድን ትናንት በግፍ የተሰዉና በደቡብ አፍሪካ የተገደሉ ወገኖች የሚታሰቡበት የሐዘን ቀን ሊታወጅ ነው። አይ ኤስ በተሰኘው አሸባሪ ቡድን ሰለባ የሆኑት ስደተኞች ኢትዮጵያውያን መሆናቸው መረጋገጡን የመንግስት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት ገልጿል።

አይ ኤስ በተሰኘው አሸባሪ ቡድን የተፈፀመው ኢ-ሰብዓዊ ድርጊት በሰው ልጅ ላይ የተፈፀመ አስነዋሪና አረመኔያዊ ድርጊት በመሆኑ መንግስት በምሬት እንደሚያወግዘው መግለጹ ይታወሳል። በአሁኑ ወቅትም የሟቾች ምስል እየተጣራ መሆኑንና ከተለያዩ አካላትም ኢትዮጵያውያን መሆናቸው መረጋገጡን ጽህፈት ቤቱ በላከው መግለጫ አስታውቋል።

የኢትዮጵያ መንግስት በንፁሃን ዜጎቻችን ላይ በደረሰው ጉዳት በእጅጉ ማዘኑን እየገለጸ ለቤተሰቦቻቸው መጽናናትን ይመኛል ብሏል። ቀጣይ በመንግስት የሚወሰዱ እርምጃዎች እንደሚገለጹና በነገው ዕለትም የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ተሰብስቦ በደቡብ አፍሪካና በሊቢያ በግፍ ለተገደሉ ዜጎች የሦስት ቀናት የሃዘን ቀን እንደሚያውጅ አስታውቋል።

በመላ አገሪቱና በኢትዮጵያ ኤምባሲዎች ሰንደቅ ዓላማ ዝቅ ብሎ እንዲውለበለብ ውሳኔ እንደሚያሳልፍም ገልጿል። መንግስት አስቀድሞ የጀመረውን የፀረ ሽብር ትግል አጠናክሮ እንደሚቀጥልና በንፁሃን ላይ የደረሰው የሽብር አደጋ ለአፍታም ቢሆን ከተጀመረው ትግል እንደማያዘናጋው ለኢትዮጵያ ህዝብ ማረጋገጥ ይወዳል ብሏል።

በዚህ አጋጣሚ መላው ኢትዮጵያውያን በፀረ-ሽብር ላይ የተከፈተውን ዘመቻ አጠናክረው እንዲቀጥሉ መንግስት ጥሪውን አቅርቧል። በኢትዮጵያ ሰርቶ የመለወጥ እድል እየሰፋ በመሆኑና በቀጣይም በህዝቦች ርብርብ ይበልጥ እየሰፋ እንደሚሄድ በመግለጫው አመልክቷል።

በመሆኑም ኢትዮጵያውያን ለጥቃት በሚያጋልጣቸው አቅጣጫ በመሄድ አደጋ ላይ ከሚጥላቸው ህገ-ወጥ ስደት እንዲታቀቡ የኃይማኖት ተቋማትና ቤተሰቦቻቸው ጠንክረው እንዲሰሩ አሳስቧል።
ምንጭ:ኢዜአ

No comments:

Post a Comment