Wednesday, March 04, 2015

በዓድዋ ጦርነት ለነጻነታችን ያሳየነው ወኔና ተጋድሎ ዛሬም በድህነት ትግሉ ሊደገም ይገባል

(Mar 04 (አዲስ አበባ))--ወራሪውን የኢጣሊያ ፋሽስት ስለረታንበት ታላቁ የዓድዋ ድል፤ ነጻነታችንን እንደጠበቅን ስለ መቆየታችን፤ ስለቀደሙት ጀግኖች አባቶቻችንና አያቶቻችን ማንነት፤ ለአገራቸው ሉዓላዊነትና ለሕዝባቸው ነጻነት ያደረጉትን አኩሪ ተጋድሎ፤ ስለጥንካሬያቸው፤ በዓለም ላይ ገኖ ስለሚነገረው ግዙፍና ገናና ታሪካቸው፤ ለአገራቸው ሲሉ ስላፈሰሱት ደምና ስለ ከሰከሱት አጥንት ለመዘከር፤ የድላቸውንና የህልፈታቸውን ታሪካዊ የመታሰቢያ በዓል ለአዲሱ ትውልድ ለመንገርና ለማስተማር ሲባል እነሆ በየዓመቱ የካቲት 23ን አገራችን ብሄራዊ በዓል አድርጋ ማክበር ከጀመረች ብዙ ዓመታት ተቆጥረዋል።

በእርግጥም ይህን ማድረጋችን ተገቢነት አለው በሚለው የአስተሳሰብ ጥጋት እንጂ ክፋት አለው በሚለው የወዲህኛው አቅጣጫ ለመነሳት በእጅጉ አልፈልግም፤ ከቶም አላደርገውም። ምክንያቱም ይህ ታሪክ የኔም፣ የነሱም፣ የእርስዎም የሁላችንም ታሪክ ነውና፤ ስለ ዓድዋ በዓል አከባበር ባሰብኩ ወቅት ሁልጊዜም ታላቅ የሆነችው የሙዚቃ ሰው እጅጋየሁ ሽባባው (ጂጂ) ምስጋና ይግባትና «ዓድዋ» የሚለው ድንቅና ለስላሳ ዜማዋ በአዕምሮዬ ይመላለስብኛል።

በዚህ ዜማዋ ውስጥ የዓድዋን ዘመን አይሽሬነትና እስከ መጨረሻው ትውልድ (የሚባል ካለ) ድረስ አይረሴነቱን በጠበቀ መልኩ መቀጠል እንዳለበት የምታስተምርበት «ዓድዋ ዛሬ ነው፤ ዓድዋ ትናንት» የሚለው የግጥም ክፍል ደግሞ ከሁሉም የዜማው ክፍሎች በተለየ መልኩ ስሜት ይሰጠኛል። በዚህ ውስጥ ታዲያ ስለብዙ ነገሮች መናገር ማንሳትና መጣል ይቻላል። በትናንቱ የዓድዋ ጦርነት ስለተገኘው ድል፤ ስለ ወደቁት ጀግኖች አባቶቻችን አጽምና ትተውት ስላለፉት ቃላቸው ወዘተ...። በመሆኑም ነጻነታቸውን በሚሹና የአልደፈር ባይነታቸው እልህና ወኔ አስገድዶ በጦር ሜዳ ስላዋላቸው የትናንቷ ኢትዮጵያ ድንቅ ልጆች ታሪክ አንስተን ዛሬም መዘከራችንን ያሳያል።

ዓድዋ ዛሬ ነው፤ በሚለው ግጥም ውስጥ ደግሞ ልብና ሕሊና ያለው የዛሬይቱ ኢትዮጵያ ትውልድ በልማቱና ድህነትን ለማሸነፍ በሚደረገው መራር ተጋድሎ ውስጥ የማይፋቅ አሻራውን በማሳረፍ ነገም፤ እስከዘላለም ድረስ ታሪካዊ የሆነውን «ድህነትን የማሸነፍ ዓድዋ» የሚዘከርበትን ታሪክ የመጻፍ ኃላፊነቱን ይወጣ የሚል ሃሳብን ያነገበ ይመስለኛል። ድህነትን የማሸነፍ ሰፊ ተጋድሎ ወራሪ ኃይልን ለማሸነፍ ከሚደረገው የጦር ሜዳ ትግል ተነጥሎ የሚታይ አይደለምና በቀጣዩ ትውልድም ሲታወስ፤ ሲዘከርና ሲከበር የሚኖር ታላቅ የታሪክ ምዕራፍ የሚሆንበት እድል ሰፊ ነው የሚል ዕምነት አለኝ። ይህን የነጻነት በዓል ማክበሩ ቅድም በመግቢያ ላይ እንዳልኩት ክፋት አለው የሚል ድምዳሜ ላይ አልደረ ስኩም፤ መነሻዬም አይደለም።

መነሻዬም ሆነ መድረሻዬም ይህን የነጻነታችን ፋና ወጊ ተጋድሎና ድላችን ለዓለም የተበሰ ረበት፤ አብዛኞቹ የአፍሪካ አገራት ማለት በሚቻልበት መልኩ ከቅኝ ግዛት ለመላቀ ቃቸው ምክንያት የሆነው ታላቁን የዓድዋ የድል ታሪክ መሰረት አድርገን ስላለፈው ነጻነታችን ብቻ ከምንናገር የምንመኘውን ከበለጸጉት አገራት ጎራ የመሰለፍ ህልማችንን እንዳናሳካ ሰንኮፍ የሆነብንን ድህነትን ለመዋጊያነት አናውልም የሚል ነው። ይህን እንድል የሚያስገድደኝ ደግሞ በታሪክ ተውጠንና በታሪክ ብቻ ተሸብበን በዘመነ ቴክኖሎጂ ስንት መስራት የምንችልበት እጃችን፣ ረጅም ርቀት ሊያስሮጠን የሚገባው እግራችን፣ ብዙ ማሰብ የምንችልበት አዕም ሮአችን በመዘናጋት የስንፍና አደጋ እንዳይጠቃ ካለኝ ስጋት በመነሳት ነው።

በየዓመቱ የሚከበረውን የታላቁን የዓድዋ ድል በዓል ስናከብር መጀመሪያችንም ሆነ መጨረሻችን የባለታሪኮቹን ረጅም ታሪክ መተረክ፤ የባለጀግኖቹን ሰፊ የጀግንነት ተጋድሎ ብቻ ማቀንቀን ላይ ማተኮሩ ተገቢ ነው የሚል እምነት ፈጽሞ የለኝም። ዛሬም እኮ ስንት የዓድዋን አይነት ጀግኖች የሚሹ ገና ያልተሻገርናቸው ፈተናዎች ከፊታችን ቆመው አላሳልፍ እያሉን ነው። ዛሬም ሰፊ የሆነውን የማደግ ብርቱ ፍላጎታችንን ከስኬት ለማድረስ የትናንት ወዲያውን አይነት የዓድዋ ትግል የሚጠይቁ ብዙ ያልተመለሱ ጥያቄዎች አሉብን፤ ዛሬም እኮ የልማታችን ፍጹም ተቃራኒና ባላንጣ የሆኑ የመልካም አስተዳደር፣ የኪራይ ሰብሳቢነት፣ስልጣንን አላግባብ የመጠቀም ዝንባሌ፣ የአድሎአዊ አሰራር፣ ሙስና ወዘተ... የዚህችን አገር ህልውና እየተፈታተኗት ነው። ስለሆነም እንደ ዓድዋው ዘመን ሁሉ ዛሬም ክተት ሰራዊት ምታ ነጋሪት ብለን በእነዚህ የዛሬ ፋሽስቶቻችን ላይ ልንዘምትባቸው ይገባል።

ዓድዋ...ዓድዋ...በሚል የታሪክ ምዕራፍ ውስጥ ብቻ ቁጭ ብለን ዜማ እየቀያየርን፣ ታሪክ እያሽሞነሞንን፣ ቅላጼ በተሞላበት የሚያስገመግም ድምጸት ብናወራ የዓድዋን ጀግኖች ወኔ የተላበሰ ስጋ በሰላም ካረፈበት መካነ መቃብር፤ ለአገርና ለወገን መልካሙን ተጋድሎ ፈጽሞ በሰላም ያረፈውን መንፈሳ ቸውን ከሰማዕታት መንደር እየቀሰቀሱ አላሳርፍ ከማለት የዘለለ ምንም ጠብ የሚል ስሙኒ አይኖርም። ይህን ሕያውና ክቡር ታሪካቸውን ለመዘከርና የነሱንም ስም ለማስከበር ብሎም ለማክበር በእጃችን ላይ የያዝናት የሰናፍጭ ቅንጣት የምታክል የስራ ታሪክ ሊኖረን ግድ ይላል።

«ዓድዋ ዛሬ ናት»
አባቶቻችን በከፈሉልን የህይወት መስዋዕትነት እልፍኝና ሰገነት ላይ ቆመን መሳጭ የሆነውን ታሪካቸውን ብናነበንብ ከንቱ ድካም ይሆንብናል። ዛሬ መስራት በምንችልበት የስራ ዘርፍና ልማትና የመልካም አስተዳደርን ማስፈን በሚቻልባቸው ጎዳናዎች ላይ በንቃት ተሳትፈን ብል የማይበላውን ነቀዝ የማያ በላሸውን የዛሬዋን እለት የዓድዋ ታሪክ መጻፍና ማጻፍ አለብን።

ታሪክ ከታሪክነቱም አልፎ ወቃሽ መሆኑን ሳስብ ምን ያህል ከባድ እንደሆነ ይገባኝና በራሴ ፍጹም አዝናለሁ። ይህንንም ልነግራችሁ እወዳለሁ! ባለታሪኮቹ በተግባር የፈጸሙትን ጠበብት ሊቃውንት ደግሞ በማይነጥፈው የታሪክ ፍሰትና የቃላት ድርድሮሽ ከትበው አቀረቡልን። እዚህ ድረስ ምንም አይነት የታሪክ መፋለስ አይታይም። ምክንያቱም ሁለቱም ባለታሪኮች ናቸው። የታሪክ ፍልሰቱ የሚጀምረው በተግባር ያልተደገፈ ታሪክ ባለን የዚህ ዘመን ሰዎች በሆነው ላይ ታሪኩ ሲወድቅ ነው። በከንቱ የመኩራራት አባዜ ተጠምደን ታሪክ ብቻ እያነበብን ለነገው ተተኪ ትውልድ የምትሆን አንዲት ታሪክ ሳንሰራ የአባቶቻችንን የድል ብስራትና የጀግንነት ውጤት የሆነውን ታሪካቸውን ስንለፍፍ ይኸኔ ነው ታሪክ ተፋለሰ ማለት። ይህን ስል ግን ዛሬም ቢሆን አገራቸውን አገራችንን በልማት የተግባር ታሪክ ጎዳና የሚያራምዱ የአብራኳ ፍሬ የሆኑ ልጆች የሉም ማለቴ ግን አይደለም። የነሱን ጎዳና እየቀደሙ እንቅፋትን የሚደረድሩ አገር ቀባሪዎች መኖራቸውን ለማመላከት ካደረብኝ ጽኑ ፍላጎት በመነሳት ነው።

አገር ቀባሪዎች ስል እጃቸውን ለመልካሙ የእድገት መሰረት አንዲት ጠጠር እንዲጥል ከማድረግ ይልቅ ከደሃው ወንድማቸው ሙስና ለመቀበል የሚዘረጉ፣ ከህዝብና መንግስት ካዝና ለመስረቅ የሚጠቀሙበት፣ መልካም ገጽታዋን ለማበላሸት የሚያገለግል ጽሁፍ ለመጻፍ ብዕር የሚጨብጡበት ጥቂት የማይባሉ የአገሬ ነቀዞች ለማለት ፈልጌ ነው። በእርግጠኝነት የነዛ የዓድዋ ጀግኖች ሰማዕታት አጥንትና ደም እንድሚፋረዳቸው አትጠራ ጠሩ። ዓድዋ ነጻነታችንን ሰጠን ነጻነታችን ደግሞ ሰላማዊ የሆነውን የኢትዮጰያዊነት አየር እንድንስብ፤ መልካም መአዛዋን እንድናሻት ረዳን። ይህ መልካም መአዛ እንዳይጠፋ መስራት ንጹህ አየሯ እንዳይበከል ማድረግ ግን አቃተን። ሰርቶ ከመብላት መቀማትና መዝረፍን፣ በአገር ለፍቶ ከማደር ይልቅ በባዕዳን አገር መሰደድን፣ በባህር ለአሳነባሪ በየብስ ደግሞ ለበረሃ አውሬ እራት መሆንን መረጥን። ዓድዋ ግን ይህ አልነበረም ከጠላት ጋር መዋደቋ ይህ አልነበረም የነዛ ጀግኖች ሰማዕታት የአደራ ቃል።

ቃላቸውን በዘመነኛ ቃል በርዘን ዓድዋን በነበረ ምስል ቀርጸን ሁሉንም ነበረ ከሚለው ቃል መጨረሻ በአራት ነጥብ እያሰርን ካለንበት ቁጭ እንዳልን አቤት ስንት ዓድዋዎች በላያችን ላይ አለፉብን? አንዳንዴ ጀግንነት ከጦርነት ጋር ብቻ ለምን እንደሚነሳ ግር ይለኛል። ቀስ ብዬ ምንጩን ሳጣራ ከጦርነት የዘለለ ገድልን መፈጸም ያቃተን መሆኑን ስረዳ በእጅጉ እገረማለሁ። በኃይማኖት መጽሐፍ ላይ እንዲህ የሚል ቃል ተቀምጧል። ንጉስ ዳዊት በሰራቸው በዛ ያሉ ኃጢአቶች ምክንያት መቀጣት ስለነበረበት «ከጦርነትና ከረሃብ በየትኛው ትቀጣ?» የሚል ጥያቄ ይቀርብለታል። እሱም ጦርነት ጊዜ የሚሰጥ መሆኑን፤ ረሃብ ግን ምንም አይነት ጊዜ የማይሰጥ መሆኑን ጠንቅቆ ያውቅ ነበረና ጦርነትን ለመምረጥ ችሏል። ታዲያ በየትኛው ላይ ድል መቀዳጀት የተሻለ ነው ትላላችሁ?

ዛሬም እኮ የዓድዋን ገድል መፈጸም የምንችልባቸው ሜዳዎች ብዙ ናቸው። ከኛ የሚጠበቀው ከታሪክ ድርሳናት ሽምደዳ መውጣት ብቻ ነው። ይህን ማድረግ ከቻልን ደግሞ ቁጥራቸው እጅግ ብዙ የሚባሉ የዓድዋ ድሎችን ማስመዝገብ የምንችልበትን አጋጣሚ ፈጠርን ማለት ነው። እነዚህን የዓድዋ ድሎቻችንን ለመፈጸም ደግሞ እንደ ከዚህ ቀደሙ ዳገት ቁልቁለት ሜዳ ተራራ መውጣትና መውረድ ፈጽሞ አያሻንም። ባለንበትና በተሰማራንበት ቦታ ሁሉ ከንቅዘት የአስተሳሰብ ስሌት ወጥተን ፍሬያማ ተግባርን ብቻ መከወን ነው የሚጠበቅብን። ይህ ደግሞ በዓድዋ የወደቁትን የመንፈስ አባቶቻችንን፤ ለአገራቸው ሉዓላዊነት፣ ለሕዝባቸው ነጻነት የከፈሉት መሥዋዕትነት ምን ያህል ታላቅ፣ ክቡርና ግዙፍ እንደሆነ ዳግመኛ በሕሊናችን ውስጥ ሊስልልንና ሊያሳየን የሚችል እንደሚሆን እርግጠኛ ሆነን መናገር እንችላለን።

እንግዲህ ይህ በፍሬ ላይ የተመሰረተ ተግባረ ህሊና ወስጋ የሚኖርበትን ብርቱ ፈተና፣ ቁጭትና የነጻነት ፍቅር በፈጠረው «ትግል ዓድዋ» ክተት ሰራዊት ምታ ነጋሪት እያሸነፍን አንዲት ታሪክ መስራት ከቻልን ስለ ትናንቱ የዓድዋ ድል ብቻ ሳይሆን ስለ ዛሬው፤ ስለ ነገውና ስለ ሁሌውም የዓድዋ ድል በስፋት ለማብሰርና ለመዘከር የምንደፍርበትን እድል በስፋት አገኘን ማለት ነው። ይህን እንድ ንፈጽምና በቀጣዮቹ የዓድዋ በዓላት ላይ የኛንም ታሪክ ቀንጭበን እንድናቀርብ፤ በእነዛ የሰማይን ጫፍ የነኩ በሚመስሉ በሰሜን ትልልቅ ተራሮች በደም የተመሰረተ፤ በትግል ላብ የነጻ፤ ከጀግኖች ሰውነት በሚወጣ መአዛ የተዋበ፤ በቃላቸው ኪዳን ለዘመናት የጸና፤ የፋሽስቶችንና የወራሪያኑን የአውሮፓውያን ቅኝ ገዢዎችን ሕልም ያጨናገፈ፤ጽኑ ኃይላቸውን የረታ፤ ሥጋንና አጥንትን ሰርስሮ ነፍስ ድረስ ዘልቆ የሚገባ ክቡርና ሕያው የጀግኖች ደጀንነት ይርዳን።

«የተሰጠኝ ሕይወት ዛሬ በነጻነት፣
ሰው ተከፍሎበታል ከደምና ከአጥንት፡፡
ምስጋና ለእነርሱ ለዓድዋ ጀግኖች፣
ለዛሬ ነጻነት ላበቁኝ ወገኖች፡፡» እጅጋየሁ ሽባባው እንዳለችው።
ምንጭ: ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment