Wednesday, March 04, 2015

የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ የግብፅን ዕይታ ቀይሮት ይሆን? « ግብፅ ከአፍሪካ አገሮች ጋር ወደ ሁሉን አቀፍ ትብብር መምጣት ትሻለች» - ፕሬዚዳንት አብዱል ፈታህ አልሲሲ

(Mar 04 (አዲስ አበባ))--ያለው የግብፅ መንግሥት አገሪቷ በአፍሪካ ህብረት፣ ከአፍሪካ ሀገሮች የሁለትዮሽ ግንኙነት ጋርም ሆነ ከሁሉም የትብብር ማዕቀፎች ጋር በላቀ ትብብር ለመስራት የተዘጋጀ ነው። በተለይም የተፈጥሮ ወንዝ ይበልጥ ካስተሳሰራቸው የናይል ተፋሰስ አገሮች ጋርም በውይይትና በትብብር ለጋራ ጥቅም ይሠራል» ይላሉ የግብፁ ፕሬዚዳንት አብዱል ፈታህ አልሲሲ።

ወቅቱ የአፍሪካ ህዝቦች ከድህነት በመውጣት ወደ ተሻለ ዕድገት ለመሄድ የሚተጉበት እንደመሆኑ ፤ የግብፅ መንግሥትና ህዝብም የራሱን ዕድገት፤ ሠላምና መረጋጋት እያረጋገጠ በአህጉሩም ተመሳሳይ ሁኔታ እንዲፈጠር ከመስራት ውጪ አማራጭ እንደሌለውም ነው የተናገሩት። በተለይ ሽብርተኝነት በአፍሪካ አህጉርም ሆነ በመካከለኛው ምስራቅ አገሮች ላይ ከሚያደርሰው ከፍተኛ ጉዳት ባሻገር የግብፅ ስጋት እንደመሆኑም ከሁሉም ሠላም ወዳድ ኃይሎች ጋር በመሆን በፅናት መታገል አስፈላጊ ነው።

ከናይል ተፋሰስና ከደቡባዊ አፍሪካ አገሮች የተውጣጡ የህትመት መገናኛ ብዙኃን ዋና አዘጋጆችና ከፍተኛ ባለሙያዎች ከየካቲት 7- 18/2007 ዓ.ም በግብፅ ጉብኝት አድርገዋል። በዚህ መርሃ ግብር ከሀገሪቷ ፕሬዚዳንት አብዱልፈታህ አልሲሲ ጋር ተገናኝተው ባደረጉት ውይይት ከተነሱ በርካታ ነጥቦች ጋር በተያያዘ «ግብፅ በናይል የውሃ አጠቃቀም የስምምነት ማዕቀፎች ላይ ያላት አቋም ምንድን ነው? በተለይ ወደ ሦስትዮሽ ውይይቱ ለመምጣት ምን አስባለች?» የሚሉና በታላቁ የህዳሴ ግድብ ግንባታ ዙሪያ የሚያጠነጥኑ ጥያቄዎች ተነስተዋል።

ፕሬዚዳንቱም «ከቅርብ ጊዜው የግብፅ ህዝብ አብዮት በኋላ ያለው መንግሥት ናይል የጋራ ሀብት እንደመሆኑ ሌሎች ሀገሮች ሊጠቀሙ እንደሚችሉ ይገነዘባል፤ ይሁንና ውሃው ለግብፅ ህዝብ የህልውና ጉዳይ በመሆኑም ጥቅማችን እንዳይጎዳ በስምምነት የመስራት አቅጣጫን ይከተላል » ብለዋል።

«የግብፅና ኢትዮጵያ የፖለቲካ አመራር አባላት በጉዳዩ ላይ ተቀራርበው መነጋገር ጀምረዋል። በቀጣይም ተጨማሪ ውይይቶችን በማድረግና የሁለትዮሽ ግንኙነቱን በማሳደግ የበለጠ መተማመን ለመፍጠር እንሰራለን» ብለው፤ ሁለቱ ሀገሮች ከሌሎች የተፋሰሱ አገሮች ጋር በመተባበር በኢነርጂ በመሠረተ ልማት፣ በቱሪዝምና ኢንቨስትመንት የሀገሮቹን ጥቅም ማረጋገጥ እንዳለባቸውም ተናግረዋል። ለዚህም በቅርቡ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በግብፅ ይፋዊ የስራ ጉብኝትና ውይይት እንደሚያደርጉ ነው የጠቆሙት።

«በአባይ ( ናይል) ወንዝ ዙሪያ ከኢትዮጵያ ጋር ያለን ስምምነት ወደ ሰነድ የምንቀይርበት ጊዜ አሁን ነው» በማለት ገልጸዋል። በግብፅ የልማት አጋርነት ኤጀንሲ፣ የውጭ ግንኙነትና አማካሪዎች ምክር ቤትና የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የስራ ኃላፊዎች ከጋዜጠኞች ቡድን ጋር በተለያዩ መድረኮች ተወያይተዋል።

የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳሚህ ሽኩሪ በበኩላቸው እንደገለጹት፤ የግብፅ መንግሥት ከአፍሪካ አገሮች ጋር በላቀ የትብብር መንፈስ በመስራት በአፍሪካ አንድነት (ህብረት) ምስረታ ወቅት ወደነበረበት ስፍራ መመለስ ይሻሉ። በዚህ ረገድ በናይል ውሃ አጠቃቀም ዙሪያ ከተፋሰሱ አገሮች ጋር በተለያዩ የትብብር መስኮች ላይ ይሰራሉ። «በታላቁ የህዳሴ ግድብ ግንባታ ዙሪያ በመተማመን ላይ የተመሰረተ ስምምነት ላይ ለመድረስ መልካም ውይይት እያደረግን ነው። በቅርቡም ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቴዎድሮስ አድህኖም ጋር ገንቢ ውይይት አድርገናል» ብለዋል።

በኢትዮጵያ የቀድሞው የግብፅ አምባሳደርና የግብፅ የውጭ ጉዳይ ምክር ቤት አባል አምባሳደር ሮበር እስክንድር በተለይ ለጋዜጣው ሪፖርተር እንደገለጹት፤ የናይል ውሃ 86 በመቶ ዋነኛ ምንጭ የሆነችው ኢትዮጵያ የጀመረችው ልማት የግብፅ ህዝብን ጥቅም እንደማይጎዳ ለመተማመን የተጀመረው ውይይትና የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት ተጠናክሮ መቀጠል አለበት። «የግብፅና የኢትዮጵያ ህዝቦች ታሪካዊና ሃይማኖታዊ ግንኙነት የነበራቸው ታላቅ ህዝቦች ናቸው። ይህን መስተጋብር በጋራ ተጠቃሚነትና መተሳሰብ በማሳደግ ለትውልድ ማስተላለፍ ይገባቸዋል» ሲሉ ገልጸዋል።

የጋዜጠኞች የልዑካን ቡድኑ አባላት ያነጋገርናቸው ሩዋንዳዊ ዊልሰን ታዊግራና ታንዛኒያዊው ገብራል ኒድ ሩማክ እንደገለጹት፤ ግብፃዊያን በብቸኝነት በሚባል ደረጃ በናይል ውሃ ለዓመታት ሲጠቀሙ መቆየታቸውን በጎበኘናቸው ቦታዎች ሁሉ ተመልከተናል። ከዚህ በኋላም ሌሎች የተፋሰሱ አገሮችም ውሃውን በቁጠባና በፍትሃዊነት እንዲጠቀሙበት ማገዝ አለባቸው።

« የግብፅ መሪዎች ከአፍሪካ አገሮች ጋር አዲስ የትብብር አጋርነት አቅጣጫን መከተል እንሻለን ሲሉ ዋነኛ ማሳያው ወደ ስምምነትና ድርድር በመምጣት የጋራ ጥቅምን ለማስጠበቅ መስራት ነው»ያሉት አስተያየት የሰጡት፤ በአፍሪካ ህብረት ውስጥ እንደ ሠላም ማስከበር፣ የፀረ ሽብር ትግልና የንግድና መሠረተ ልማት ተግባራት ላይም በንቃት መሳተፍ እንደሚኖርባቸው ተናግረዋል።

ከኢትዮጵያ ልዑካን ቡድን አባላት አንዱ የዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከል ዌብ ሳይትና ሞኒተሪንግ ዋና ክፍል ኃላፊ ሞላ ምትኩ በበኩላቸው እንደሚሉት፤ የግብፅ ፖለቲከኞች በታላቁ ህዳሴ ግድብ ጉዳይም ሆነ በመላው የተፋሰሱ ሀገሮች ፍትሃዊና ምክንያታዊ የውሃ አጠቃቀም ላይ ግልፅ አቋም ይዘው መስራት አለባቸው፤ በተለይ ለህዝባቸው ተጨባጩን እውነት በማስረዳት ለጋራ ተጠቃሚነት የማነሳሳቱን ስራም ትኩረት መስጠት አለባቸው።

የግብፅና የአፍሪካ ግንኙነትን ለማሻሻል፣ ድህረ አብዮት እየተፈጠረ ላለው የመንግሥት አቋም የተፋሰሱ ሀገሮች የውሃ ስምምነት ማዕቀፍ ማፅደቅና የታላቁ ህዳሴ ግድብ አይነት ፕሮጀክቶች መጀመር ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንደሚያደርግም የገለጹ ተሳታፊዎች አሉ።

በ12 ቀናት በግብፅ ካይሮና አስዎን ግዛት የተካሄደው የመስክ ጉብኝት በሀገሪቷ የውሃ አጠቃቀም፣ በታሪካዊና ሃይማኖታዊ የቱሪስት መስህብ ስፍራዎች ላይ ያተኮረ ሲሆን፤ ከኢትዮጵያ፣ ሱዳን፣ ታንዛኒያ፣ ኡጋንዳ፣ ኤርትራ፣ ዛምቢያ፣ ዚምባቢዌ፣ ሞዛምቢክ፣ ኬንያ፣ ናምቢያ፣ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ ብሩንዲ ፣ ደቡብ ሱዳን፣ አንጎላና ሩዋንዳ የተገኙ 28 ዋና አዘጋጆችና ከፍተኛ ደረጃ ላይ የሚገኙ ጋዜጠኞች ተሳትፈዋል።
ምንጭ: ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment