Tuesday, March 31, 2015

«ግድቡን በተባለው ጊዜ ለማጠናቀቅ ከፍተኛ ርብርብ ይደረጋል»- ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ

(መጋቢት 22, 2007, (አዲስ አበባ))--ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ሰሞኑን ለአገር ውስጥ ጋዜጠኞች በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ ማብራሪያ ሰጥተዋል። በዚሁ ወቅት ከተነሱት ጥያቄዎች መካከልም ኢትዮጵያና ግብፅን የተመለከቱት ጉዳዮች ሚዛኑን ይደፋሉ። ሁለቱ አገራት በአባይ ወንዝ ፍትሐዊ አጠቃቀም የተነሳ በጥርጣሬ ላይ የተመሰረተ ግንኙነት ነበራቸው።

ከዚህ የጥርጣሬ ግንኙነት ተላቅቀው ሰሞኑን ሦስቱ አገሮች ያደረጉትን የመርህ ስምምነት ተከትሎ የግብፅ ፕሬዚዳንት በኢትዮጵያ ለሦስት ቀናት ይፋዊ ጉብኝት አድርገዋል። ፕሬዚዳንቱ በቆይታቸው ከኢትዮጵያ ጋር በተለያዩ መስኮች በትብብር ለመስራት የሚያስችል ስምምነት አድርገው ተመል ሰዋል። በእዚህ ጉዳይ ላይና በሌሎች ጉዳዮች ዙሪያ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ሰፋ ያለ ማብራሪያ ነበር የሰጡት። የማብራሪያውን ሦስተኛ ክፍልም ለዛሬ እንዲህ አቅርበነዋል።

የኢትዮጵያና የግብፅ ግንኙነት በአባይ ወንዝ ላይ ብቻ የተመሰረተ አይደለም። አክራሪነት በአካባቢያችን ከፍተኛ ችግር ነው። መላው ዓለምም በአክራሪነት እየተናጠ ነው። በኢትዮጵያ አካባቢ አልሸባብ፤ በግብፅ ደግሞ የሊቢያን አለመረጋጋት ተከትሎ የአይ ኤስ ኤስ ስጋት፤ እንዲሁም በናይጄሪያ ቦኮሀራም አለ። አልቃይዳ በየመን ከፍተኛ ችግር እያደረሰ ነው። እነዚህ በሙሉ አክራሪነትንና ሽብርተኝነትን በጋራ መታገል እንዳለብን የሚያመለክቱ ስለሆነ ስምምነት ላይ ደርሰናል። ይህ አንድ እርምጃ ነው። የኢኮኖሚ ልማትና ኢንቨስትመንት ለማጠ ናከር እንዲሁም የአካባቢያዊ ውህደትን ለማቀላጠፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረክታል።

ግብፅና ኢትዮጵያ በመዋዕለ ንዋይ ለመተሳሰር ያደረጉት ስምምነት ሌላው ተጠቃሽ ጉዳይ ነው። በዚህ መሰረት የግብፅ ባለሀብቶች በአገሪቱ የኢንዱስትሪ ፓርክ ለማቋቋም አስበዋል። በተለይም ጉልበትን በሰፊው በሚጠቀሙ ቀላል ኢንዱስትሪዎች ዙሪያ የተጀመረ ሥራ አለ። ኢትዮጵያ ካላት እምቅ ሀብትና ከግብፅ ፍላጎት አንጻር በግብርና መስክ ሁለቱ አገራት የንግድ ልውውጥ ለማድረግ አቅደዋል። በዚህ ረገድ የእንስሳት ተዋጽኦን በተለይ ሥጋ በብዛት ወደ ግብፅ ለመላክ ታስቧል።

የህዝብ ለህዝብ ግንኙነቱን ማጠናከር የሁለቱ አገራት ሌላው ስምምነት ነው። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን እና የግብፅ ኮፕቲክ ቤተክርስቲያን እንዲሁም የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ከግብፅ ጋር በጥብቅ ትስስር የሚፈጥሩበትና የህዝብ ለህዝብ ግንኙነቱን የሚያጠናክሩበትን ሁኔታ ለማመቻቸት ታቅዷል። በባህላዊ ሙዚቃ፣ በኪነ ጥበብ እና በስፖርት መስኮች የልምድና የልዑካን ቡድንን ልውውጥ በማድረግ የህዝብ ለህዝብ ግንኙነታችንን የማጠናከር ስምምነቶች ተካሂደዋል።

የቱሪዝምን ሀብት የጋራ ተጠቃሚነትን በሚያሰፋ መልኩ ለመጠቀም ሁለቱ አገራት ስምምነት ላይ ደርሰዋል። በእዚህ መሰረት ኢትዮጵያን የሚጎበኙ ቱሪስቶች ግብፅን እንዲሁም የእነርሱን አገር የሚጎበኙ ወደ ኢትዮጵያ የሚመጡበትን ስልት ለመንደፍ ተስማምተናል። የአውሮፕላን በረራን በሁለቱም ወገን ለማሳደግ፤ የየብስ ትራንስፖ ርት፣ ባቡር እንዲሁም በኃይል መሰረተ ልማት ከወዲሁ ግብፅን፣ ኢትዮጵያንና ሱዳንን ለማስተሳሰር እንዲሁም ወደ ሜዲትራንያን ባህር የሚወስደውን መንገድ ማሳጠር በሚቻልበት ስልት ስምምነት ተደርሷል።

የምርምርና የከፍተኛ ትምህርት ግንኙነትን የበለጠ ማጠናከር ይገባል የሚለው በአገራቱ መካከል የተደረገው ሌላው ስምምነት ነው። የግብፅ ፕሬዚዳንት በኢትዮ ጵያ ቆይታቸው ለ300ተማሪዎች ነጻ የትምህርት ዕድል ሰጥተዋል። ይህ በሁለተኛ እና በሦስተኛ ዲግሪ የተገኘው ነጻ የትምህርት ዕድል ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት በምትፈልገው የሳይንስና የቴክኖሎጂ መስኮች እንዲሆኑ ስምምነት ላይ ተደርሷል።

በኢትዮጵያና በግብፅ መካከል ከተደረጉት ስምምነቶች መካከል በካንሰር በተለይ በህጻናት ካንሰር ባለሙያዎችን ለማሰልጠን የተደረገው ስምምነት ግምት የሚሰጠው ነው። በእዚህ መስክ ሰልጣኞችን ተቀብሎ ከማስተማር ባሻገር በምርምር ዘርፍ ግብፅ ኢትዮጵያን የምትደግፍበት መንገድ ላይ ስምምነት ተደርጓል።

ኢትዮጵያና ግብፅ በአጠቃላይ በንግድ፣ በመዋዕለ ንዋይ፣ በትምህርት፣ በምርምር፣ በህዝብ ለህዝብ ግንኙነት፣ በባህልና በቱሪዝም ለመተባበር ያደረጉት ስምምነቶች እየተጠናከሩ ሲመጡ፤ ከአባይ ባሻገር ትልቁን የጋራ ግንኙነት የሚያጠናክሩ ይሆናሉ። ስምምነቶቹ ሁሉን አቀፍ በመሆናቸው በመካከል የነበሩ ጥርጣሬዎችን በማስወገድ ያለውን መተማመን የበለጠ ያጠናክሩታል።

ግብፅ በአባይ ወንዝ ላይ የነበራት አቋም ለዘመናት ሳይቀየር ወይም ሳይለሳለስ ኖሯል። የውሃውን አብዛኛው መጠን ለእኔ ይገባኛል ለዚህም ታሪካዊና ህጋዊ መብት አለኝ የሚል አመለካከት ታንጸባርቅ ነበር። ይሁንና በቅርቡ በሱዳን ካርቱም በግብፅ፣ ኢትዮጵያና ሱዳን በተደረገው የመርህ ስምምነትና በማግስቱ ወደ አዲስ አበባ ለይፋዊ ጉብኝት የመጡት የግብፁ ፕሬዚዳንት አብዱል ፈታ አል ሲሲ ለህዝብ ተወካዮች እና ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ያደረጉት ንግግር በአባይ ወንዝ ፍትሐዊነት እና ምክንያታዊነት የተላበሰ አጠቃቀም አዲስ ምዕራፍ እንዲከፈት የሚያመላክት ንግግር አድርገዋል። ለመሆኑ ይህ የግብፅ አቋም ለውጥ ከምን መነጨ? ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም የሰጡት ምላሽ ይህን ይመስላል...

ይህ የአቋም ለውጥ ጥበብ የተሞላበት ውሳኔ ነው። እዚህ ውሳኔ ላይ ለመድረስ ሁለት ምክንያቶች አሉ ብዬ አስባለሁ። የመጀመሪያው ኢትዮጵያ ግድቡን መስራት እንደማታቆም እና የማይቀለበስበት ደረጃ መድረሱን መረዳታቸው ነው። ግድቡ አራት ዓመት ሆኖታል። 42 በመቶ ተጠናቋል። ከእዚህ በኋላ እንደማይመለስ እርግጠኛ ሆነዋል። አዋቂ መሪ በዚህ ጊዜ ማድረግ የሚመርጠው ማግኘት የሚገባውን ጥቅም ማሰብ ነው። በእርግጥ እኛ በመርህ ላይ ተመስርተን እየሰራን ነው።

ጉልህ ጉዳት እንደማያደርስ ድርድር እና ስምምነት ማድረግ አለባቸው። በመኮራረፍ እና ዳር በመቆም ምንም ማድረግ እንደማይቻል ስለተረዱ በመቀራረብ፣ በመደራደር፣ በመተማመንና በመረዳዳት ላይ በመስራት አንዳችን የአንዳችንን ስጋት እና ጥቅም በሚገባ በመረዳት ፍላጎታችንን በማጣጣም ልንሄድ እንደምንችል የኢትዮጵያን አቋም ስልተረዱ ነው ወደ ስምምነቱ የመጡት።

ከፕሬዚዳንት አል ሲሲ ጋር ማላቦ ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ ከተገናኘን በኋላ አምስት ጊዜ ያህል ተከታታይ ውይይት አድርገናል። በእነዚህ ሁሉ ግንኙነቶች የኢትዮጵያ አቋም አንድ፣ የማይቀርና ግልጽ ነበር። ግድቡ እንደማይቆምና የሚይዘው የውሃ መጠን እንደማይቀንስ ተረድተዋል። ይህንን ሲረዱ ያላቸው አማራጭ ኃይል በመጠቀም ማስቆም ወይም ወደ ዲፕሎማሲና ፖለቲካዊ ውይይት መምጣት ነው። በኃይል ማስቆም እንደማ ይቻል ደግሞ በደንብ ተረድተዋል፤ ስለዚህ ያለው አማራጭ መወያየት፣ መደራደርና ወደ ስምምነት መምጣት ነው።

ሱዳን በዚህ ጉዳይ ላይ ያላት አቋም ወደ ድርድር ያመጣቸው ሁለተኛው ምክንያት ነው። ሱዳኖች በራሳቸው ምክንያት ይህ ግድብ ከማንም በላይ እኛን ይጠቅማል የሚል አቋም ይዘዋል። ይህንን መቀየር እንደማይችሉ ተረድተዋል። ሁለቱ አገሮች በግድቡ ጥቅም ከተስማሙ እኛም ከግድቡ የሚገኘውን ጥቅም ማግኘት አለብን ብለው የወሰኑ ይመስላል። በእነዚህ ሁለት ምክንያቶች ድርድር አማራጭ የለውም ብለው አምነው መጥተዋል። ትክክለኛ ውሳኔ ነው። ለአገራቸው፣ ለህዝባቸው እንዲሁም ለናይል ተፋሰስ አገራት ሁሉም አሸናፊ ሆኖ የሚወጣበትን መንገድ መርጠዋል። የግብፅ አቋም ወደ ዲፕሎማሲያዊ፣ ፖለቲካዊና ቴክኒካዊ ግንኙነት ማዘንበሉ ጥበብ የተሞላበት ውሳኔ ነው የሚል እምነት አለኝ።

የታላቁ ኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ በታቀደው መሰረት እየተከናወነ ነው። ለእዚህ መንግሥት፣ ህብረተሰቡ እንዲሁም በግንባታ ላይ የሚሰሩ በርካታ ሰዎች ርብርብ ሚና ወሳኝ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም በእዚህ ጉዳይ ዙሪያ የሚከተለውን ብለዋል ... በአፍሪካ ትልቁ በዓለም ደግሞ ዘጠነኛ ደረጃ ይይዛል ተብሎ የሚጠበቀው የታላቁ ኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ግንባታ 42 በመቶ ደርሷል። ይህ ስኬት በመላው የኢትዮጵያ ህዝብ፣ በመንግሥት፣ ግድቡን የሚገነቡ አካላት ባደረጉት ተሳትፎ የተገኘ ነው። 24 ሰዓት በመትጋት ነው ለዚህ የተደረሰው። ይሄ መንፈስ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ማድረግ ይገባል።

አራተኛ ዓመቱን ስናከብር የኢትዮጵያ ህዝብ የገባውን ቃል በማደስ መሆን አለበት። ሁሉም ትኩረቱን በማድረግ የራሱን አስተዋጽኦ በማበርከት ሥራው እስኪጠናቀቅ መተባበር አለበት። ይህን ለማድረግ የኢትዮጵያ ህዝቡ ዝግጁ ነው። መንግሥትም ለማስተባበር ዝግጁ ነው። በእቅዱ መሰረት ምንም ዓይነት መስተጓጎል ሳይገጥም እንዲጠናቀቅ ማድረግ ይገባል። በእዚያ አካባቢ የሚሰሩ ኢትዮጵያውያንና የሌሎች አገራት ዜጎች ተጠናክረው እንዲሰሩ ማበረታታት ይገባል። አራተኛ ዓመቱን ስናከብር በድል ነው። ይህ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ግድቡን በተባለው ጊዜ ለማጠናቀቅ ከፍተኛ ርብርብ ይደረጋል።

የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ የመጀመሪያው ምዕራፍ በተያዘው ዓመት ይጠናቀቃል። በዚህ ጉዳይ ላይ ጠቅላይ ሚኒስርት ኃይለማርያም የሚከተለውን አስተያየት ሰጥተዋል።  የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ የአራት ዓመት ተኩል አፈጻጸም በደንብ ተገምግሟል። በእዚህ ላይ ተመስርቶ የሁለተኛው ምዕራፍ የዕድገትና ትራንስፎር ሜሽን ረቂቅ እቅድ ተዘጋጅቷል። አፈጻጸሙን ሆነ ረቂቅ እቅዱን በተመለከተ ከሚያዝያ ጀምሮ ከዜጎች ጋር ውይይት ይደረጋል።
ምንጭ: ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ 

No comments:

Post a Comment