Wednesday, February 04, 2015

የማንነት ጥያቄ በ «ኦሮማይ» መጽሐፍ

(ጥር 26/2007, (አዲስ አበባ))--ዓመቱን ጠብቆ እንደሚመጣ በዓል በኢትዮጵያ ሥነ ጽሑፍ ውስጥ ስሙ በየጊዜው ይነሳል። የብዙዎች መነጋገሪያ የሆነ ደራሲም ነው። እርሱ በመጽሐፉ ምክንያት በሞት ቢለይም ዛሬ ድረስ ስሙ ይዘከራል - ደራሲና ጋዜጠኛ በዓሉ ግርማ።

በወርሃ መስከረም 1931ዓ.ም የተወለደው ደራሲው ትውልድና እድገቱ በኢሉአባቦራ ዞን «ሱጵዬ» በተባለች ትንሽ መንደር ውስጥ እንደሆነ መረጃዎች ያሳያሉ። አባቱ ከሕንድ «ጉጅራት» ከሚባል አካባቢ የመጡ ሲሆን፤ እናቱ የኦሮሞ ባለሀብት ልጅ ነበሩ። እስከ አሥር ዓመቱ በትውልድ መንደሩ ከተማረ በኋላ በአስር ዓመቱ ወደ አዲስ አበባ መጣ። በአዲስ አበባ ዘነበወርቅ የመጀመሪያ ደረጃ አዳሪ ትምህርት ቤት ተምሯል። ቀጥሎም ጀኔራል ዊንጌት፤ ያንን እንደጨረሰም ወደ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በመግባት በጋዜጠኝነትና ፖለቲካል ሳይንስ በ1955 ዓ.ም በመጀመሪያ ዲግሪ ተመርቋል።

ጥቂት ዓመታት እንደሰራም ወደ አሜሪካ በመሄድ በጋዜጠኝነትና በፖለቲካል ሳይንስ የሁለተኛ ዲግሪውን ከሚቺጋን ዩኒቨርሲቲ አግኝቷል። ከአድማስ ባሻገር፣ የህሊና ደውል፣ የቀይ ኮከብ ጥሪ፣ ደራሲው፣ ሀዲስና ኦሮማይ የተሰኙት መጻሕፎቹ ለሕዝብ ያበቃቸውና ከፍተኛ ዝናን ያስገኙለት የጥበብ ሥራዎቹ ናቸው።

በእነዚህ የሥነጽሑፍ ሥራዎቹ ከእዚህ ቀደም 25 የተለያዩ ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበው ለሕዝብ መነጋገሪያ ሆነዋል። በቅርቡም «በዓሉ ግርማና የኢትዮጵያ ሕዝቦች የማንነት ጥያቄ ʿኦሮማይʾ ውስጥ እንደተንጸባረቀው» በሚል በኦሮማይ ልቦለድ መጽሐፉ ላይ አንድ ጥናታዊ ጽሑፍ ቀርቦ በዘርፉ ባለሙያዎች ሂስ ተሰጥቶበታል።

በዚህ የደራሲው የጥበብ ሥራ ላይ የዘርፉ ባለሙያዎች፣ ጥሪ የተደረጋላቸው እንግዶች ትኩረት ሰጥተው እንዲወያዩ መድረኩን ያዘጋጀው በባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የኢትዮጵያ ብሔራዊ የባህል ማዕከል ነው። በዕለቱ ለውይይት የሚሆን የመነሻ ጥናት ያቀረቡት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ አምቦ ዩኒቨርሲቲና ሪፍት ቫሊ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ በማስተማር ላይ የሚገኙት ረዳት ፕሮፌሰር አቶ ተፈሪ ንጉሴ ናቸው።

የዛሬ 33 ዓመት መጽሐፉ እንዲጻፍ ምክንያት የሆነው የቀይ ኮከብ ጥሪ ዘመቻ እንደሆነ ነው የገለጹት። ያኔ በዓሉ ግርማ አስመራ የነበረ ሲሆን፣ በእዚያ ያየውንና የሰማውን መነሻ በማድረግ እንደጻፈው ጥናታዊ ጽሑፉን ባቀረቡበት ወቅት ጠቅሰዋል።

የጽሑፉ አቅራቢ በኦሮማይ ልቦለድ ውስጥ የማንነት ጥያቄ ምን ይመስላል? የሚለውን ነው በስፋት የተነተኑት። እርሳቸው «ማንነት» በመጽሐፉ ውስጥ ትልቅ ቦታ አለው ባይ ናቸው። ኢትዮጵያዊነትና ኤርትራዊነት በብዛት ተንጸባርቋል። ከእዚህ ውጪ የተወሰኑ የማንነት ጥያቄዎችም መነሳታቸውን ነው የጠቆሙት። በዓሉ ግርማ ለብሔር ብሔረሰቦች መብት መከበር ትልቅ ቦታ ሰጥቷል በድርሰቱ። በመጽሐፉ ውስጥ አማራ፣ ትግሬና ኦሮሞን ለመወከል ያደረገውን ጥረት በምሳሌነት አንስተዋል።

የኤርትራ የማንነት ችግር መነሻው ከውጭ እንደሆነ የገለጸውም «ዓረቦች ቀይ ባህርን የዓረብ ባህር የማድረግ ፍላጎት ነበራቸው። እንግሊዝና ሌሎች ምዕራባውያን ይህን ስትራቴጂክ ቦታ ለመያዝ ያላቸው ፍላጎት እንጂ ከውስጥ የፈለቀ የኤርትራ የራሷ ችግር አይደለም» በማለት ነው።

የኤርትራ ማንነት እንዲሁ ከውስጥ የፈለቀ አለመሆኑንና ከተቃዋሚዎች አንጻር የሚቀርበው የኤርትራ ማንነት የ60ዓመት የልዩነት ታሪክ መሆኑን ለማስረዳት ሞክረዋል። ከዚያ ይልቅ የኤርትራና የኢትዮጵያን ሕዝብ ለዘመናት የነበረ አንድነት የሚያሳዩ ብዙ ነገሮች በመጽሐፉ ውስጥ አሉ ባይ ናቸው።

የመሀል አገርና ኤርትራውያን የሚሉ ማንነቶች በመጽሐፉ ውስጥ በስፋት መታየታቸውንም አቶ ተፈሪ አንስተዋል። ኤርትራውያንና ኢትዮጵያውያን «እኛ እነሱ» የሚባባሉበት ብዙ ነገሮች አሉ። ቡድኖችን በጥቅል የመፈረጅ ሁኔታም እንዲሁ። ገጸ ባህሪያት ኤርትራውያን ወይም ኢትዮጵያውያን «እንዲህ ናቸው» ብለው በጥቅል ሲፈርጁ ተስተውለዋል።

ጥናት አቅራቢው እንደምሳሌ ያቀረቡት በመጽሐፉ ገጽ 271 ፍሬው ዘሪሁን የተባለ ገጸባህሪ ለፀጋዬ ስለኤርትራ ሴቶች «...ስማ ልንገርህ የአስመራ ሴቶች ጥቅምና ጉራ ነው እንጂ ፍቅር የሚባል ነገር አያውቁም። የሚወዱህ መስለው ቢታዩህ እውነት አይምሰለህ...» በማለት የተናገረውን ነው። በእዚህ ላይ የኤርትራ ሴቶች በሙሉ መጥፎ ናቸው ብሎ ሲደመድም ይታያል። በአንጻሩ የአዲስ አበባ ሴቶችን ያቀረበው ደግሞ « የአዲስ አበባ ሴቶች ይምጡብኝ አቦ። ከመልክ መልክ፣ ከጸባይ ጸባይ የታደሉ እመቤቶች ናቸው። ከወደዱህ ይወዱሀል። ከጠሉህም ያንኑ ያህል ነው። ከጥቅም ፍቅርን ያስቀድማሉ» በማለት ነው። ሁሉም የአዲስ አበባ ሴቶች እንዲህ ናቸው ብሎ መደምደሙ ጥቅል ፍረጃ እንደሚያ ሰኘው ነው ያብራሩት።

ጥናት አቅራቢው በሁለቱ አገራት መካከል ያለው ማንነት የ60ዓመታት ልዩነት ሳይሆን ለሺ ዓመታት አብሮ በመኖር የተገነባው የወል ማንነት እንደሚበልጥ ተከስተ የተባለውን ገጸባህሪ ንግግር ዋቢ በማድረግ አመላክተዋል።

በዓሉ በእዚህ ልቦለድ ውስጥ በጊዜው የኢትዮጵያን ነባራዊ ሁኔታ ፍንትው አድርጎ እንዳሳየም ነው የገለጹት። ያኔ በኢትዮጵያ ለነበረው ችግርም መፍትሔ ጠቁሟል ባይ ናቸው። ለብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ማንነት እውቅና መስጠት አንዱ ነው። እርሱ እውቅና የሰጠው በመጽሐፉ ውስጥ ያሉ ገጸባህርያት ሥሞች የብሔር ብሔረሰቦች ተዋጽኦን ያካተተ እንዲሆን በማድረግ ነው። ለተለያዩ ቋንቋዎችም ክብር በመስጠት እርስ በርስ በመከባበርና በመፈቃቀድ ላይ የተመሠረተ ግንኙነት መኖር እንዳለበት አስተምሯል።

በዓሉ ግርማ ለልዩነት እውቅና እንድንሰጥ፣ መቻቻልን እንድናጎለብትና ብዝሀነትን እንድንቀበል በመጽሐፉ ውስጥ አስተምሮናል የሚሉት አቶ ተፈሪ፤ ደራሲው በመጽሐፉ ውስጥ «የድንኳን ከተማው ሺ ደመራ ተደምሮ የተከፋፈለበት መስሏል። ጭፈራውና ዘፈኑ ይቀልጣል። እዚህ ትግሬ እዚያ የአማራ፤ ወዲህ የኦሮሞና ወዲያ የጉራጌ ዘፈኖች። ቀዝቅዝ ያለው አየር ከዘፈኑና ከጭፈራው ጋር ተዳምሮ መንፈስን ያድሳል» ሲል የገለጸውን በልዩነት ማመንና መደሰት እንደሚቻል በወቅቱ ያሳየበት እንደሆነ ጠቅሰዋል። በዓሉ ግርማ በመጽሐፉ ውስጥ በጊዜው የነበረውን የአገራችን ችግር ከእነመፍ ትሔው ያመላከተ፣ ከግለሰባዊ ማንነት እስከ ቡድን ማንነት ያንጸባረቀና ለእኩልነት የሚሟገት ደራሲ እንደነበረም አውስተዋል።

ከአጻጻፍ አንጻር ሚዛናቸውን ጠብቀው የተደረደሩ አጫጭር ዓረፍተነገሮችን መጠቀሙ መጽሐፉን ሳቢና ተወዳጅ እንዳደረገውም አንስተውለታል። ውስብስብ ሃሳቦችን ለተራ ሰውና ለማንም በቀላሉ እንዲገባ አደርጎ የማቅረብ ችሎታውንም አቶ ተፈሪ አድንቀዋል። ይህም ለመጽሐፉ ትልቅነት አንዱ ማስረጃ እንደሆነ ነው የገለጹት። የምሰላ ዘዴው፣ ነገሮችን በምጸት የሚገልጽበት ሁኔታ እንዲሁም ዘይቤያዊ ቃሎቹና ዓረፍተ ነገሮቹ የመጽሐፉን የጥበብ ምጡቅነት ያሳያል ባይ ናቸው። «ደራሲው ገጸባህሪያትን ሲስል በእውነቱ ዓለም ለሚታወቁ ሰዎች በጣም የቀረበ አድርጎ ስለሚያቀርብ በእዚህ አይረሳም» ሲሉም ነው የገለጹት።

መድረኩ ላይ የተገኙ ታዳሚዎችም ኦሮማይን ከማንነት አንጻር ተንትኖ በቀረበው በእዚህ ጥናታዊ ጽሑፍ ላይ የራሳቸውን አስተያየት ሰንዝረዋል። በጥናታዊ ጽሑፉ የበዓሉን ሥራዎች ዳግም መለስ ብለው እንዲያስቡና ከተለያየ አቅጣጫ ማየት እንደሚቻል ግንዛቤ ማግኘታቸውን ነው የገለጹት። ይሁንና ደራሲው ኦሮማይን የጻፈው በወቅቱ በጦርነቱ ካየውና ከተገነዘበው ተነስቶ በመሆኑ መጽሐፉ ልቦለድ ነው ወይስ ሪፖርታዥ? የሚል ጥያቄ አዘል አስተያየት ተነስቷል።

የተወሰኑት ደራሲው በወቅቱ የሆነውን ነገር በትክክል ያስቀመጠበትና ገጸባህርያቱም ስማቸው ተቀይሮ ከማቅረቡ ውጪ በወቅቱ የነበሩ ሰዎች ስለነበሩ ታሪካዊ ልቦለድ ቢባል የተሻለ ነው ሲሉ፤ በሌላ ወገን መጽሐፉ ታሪካዊ ልቦለድ አይደለም። ያኔ በወቅቱ የሚጻፉ ልቦለዶች በወቅቱ ያለውን ሁኔታ ነው የሚያወሱት። ዛሬ ላይ ሆኖ ሲታይ ታሪካዊ ልቦለድ ቢመስልም በወቅቱ ሲጻፍ ልቦለድ ነው የሚል አስተያየት ያቀረቡ አሉ።

በዓሉ በወቅቱ የዘመኑን ገጽታ ያንጸባረቀበት በመሆኑ ሪፖርታዥ ይምሰል እንጂ ብዙ የፈጠራ ሥራዎች ስላሉበት ሪፖርታዥ እንዳልሆነ ማሳመኛ ሃሳብ ቀርቧል። የኋላ ኋላም መጽሐፉ በአብዛኛው በኤርትራውያንና ኢትዮጵያውያን ላይ ያተኮረና በወቅቱ ያለውን ሁኔታ በተጨባጭ ያንጸባረቀ በመሆኑ ለእውነት የተጠጋ ልቦለድ አሊያም ታሪካዊ ልቦለድ ቢባል የተሻለ መሆኑን ብዙዎች ተስማምተውበታል።

በዓሉ ግርማ በኦሮማይ መጽሐፍ ላይ በኢትዮጵያውያንና በኤርትራውያን መካከል ያለው የማንነት ጥያቄ በቀላሉ ሊበጠስ እንደማ ይችል በጽሑፉ ማንጸባረቁንም ተወያዮቹ ይስማማሉ። ለእዚህም ዛሬ በሁለቱ አገራት መካከል የድንበር ልዩነት ቢኖርም በሕዝቦቹ መካከል በተለይ በውጭ በሚኖሩ የሁለቱ አገራት ዜጎች ውስጥ አንድነት መኖሩን በምሳሌነት አቅርበዋል።

በዓሉ ግርማ በሥራዎቹ የኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማርያምን ግብታዊ ወሳኔዎች (እርምጃዎች) አስመልክቶ ምንም አለማለቱን ተነስቷል። በአንጻሩ ሌሎቹን ባለሥልጣናት ለሆዳቸው ብቻ የተገዙ፣ ለአገር ደንታ የሌላቸውና ሥነምግብር የሌላቸው አድርጎ ያቀርባል። ይህ ምንም እንኳ ኮሎኔል መንግሥቱን በድፍረት ባይናገርም ባለሥልጣናት መጀመሪያ ለሰው ልጆች ልዩ ከበሬታ እንዲሰጡ ጽኑ ፍላጎት እንዳለው ያሳያል። መሬት ከመውደድ ይልቅ ቅድሚያ የሰውን ልጅ መውደድ ማስቀደም ያስፈልጋል እያለ ስለመሆኑ አስተያየት ሰጪዎቹ አንስተዋል። የሰውን ፍላጎት ለይተን እናዳምጠው የሚል ሃሳብ እንዳለም እንዲሁ።

ደራሲው ለሰው ልጆች ማንነት ልዩ ከበሬታ እንዳለው ተነስቷል። ብሔር ብሔረሰቦች እርስ በርስ መከባበር እንዳለባቸውና አገሪቱ የሁሉም መሆኗን ኪነጥበባዊ በሆነና በሚስብ መንገድ ማስቀመጡን ነው ብዙዎቹ የተስማሙበት።

በአጠቃላይ በዓሉ ግርማ በኦሮማይ መጽሐፉ እውነተኛ ታሪክን ሚዛናዊ በሆነ መንገድ ያቀረበበት ከመሆኑ በተጨማሪ ለመከበር ሌሎችን ማክበርና እርስ በርስ መዋደድ እንደሚገባ በተጨባጭ አሳይቷል። የራሱን ሚዛናዊ ማንነቱን ከማንጸባ ረቁም በላይ ሰው በሰውነቱ ብቻ መከበር አለበት የሚል አቋሙን በግልጽ ያሳየበት ስለመሆኑ በውይይቱ ላይ ተነስቷል።

የጽሑፉ አገላለጽ፣የቃላት ቁጥብነቱና የጭብጥ መረጣው ሊደነቅ ይገባል። በወቅቱ የብሔር ብሔረሰቦች ጭቆና እንደነበር ከማሳየቱ በተጨማሪ እርስ በርስ በመፈቃቀድ ላይ የተመሠረተ መዋደድ መኖር እንዳለበት አንጸባርቋል። ለባህል፣ ለቋንቋና ለብሔር ብሔረሰቦች ልዩ ከበሬታ አለው። ልዩነትን በመቻቻል ማስተናገድ እንደሚገባም መጽሐፉ አሳይቷል። ይሁንና የኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማርያምን ድክመት በድፍረት ለማንሳት አለመፈለጉ መጽሐፉን በደካማ ጎን አስነስ ቶታል።
ምንጭ: ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ 

No comments:

Post a Comment