Monday, February 09, 2015

«የውጭ አገር ዜግነት ያላቸው በኢትዮጵያ ፖለቲካ መሣተፍ አይችሉም» ► ምሁራን

(የካቲት 2/2007, (አዲስ አበባ))--«በኢትዮጵያ ህግና መርህ መሰረት ማናቸውም ትውልደ ኢትዮጵያዊ የሆኑ የውጭ አገር ዜግነት ያላቸው ሰዎች በአገሪቷ የፖለቲካ ተሳትፎ ለማድረግ ፓርቲ የመመስረት፣ አባል የመሆንና በፓርቲው ውስጥ የፈለጉትን እንቅስቃሴ የማድረግ መብት እንደሌላቸው በህግ የተደነገገ ነው» ሲሉ ምሁራን ገለጹ። ማንኛውም የፖለቲካ ፓርቲ ከውጭ አገር ዜጎችም ሆነ ከውጭ አገር መንግስት እና የፖለቲካ ድርጅቶች ስጦታ፣ እርዳታና የመሳሰሉትን መቀበል እንደማይችሉ ጠቆሙ።

በኢትዮጵያ ሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ የአመራርና መልካም አስተዳደር ኢንስቲትዩት ምክትል ዳይሬክተር አቶ መብርሃቱ ወልዱ ከጋዜጣው ሪፖርተር ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ እንደተናገሩት፤ ትውልደ ኢትዮጵያዊ የሆኑ የውጭ አገር ዜግነት ያላቸው በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ገብቶ የፖለቲካ ፓርቲ መመስረት፣ አሊያም በፓርቲው ውስጥ አባል ሆኖ መንቀሳቀስ አይችሉም። በተጨማሪም መምረጥም ሆነ መመረጥ እንደማይችል ህጉ በግልፅ ደንግጓል።

«የውጭ ዜግነት አለው ሲባል ዜግነቱ የሌላ አገር ሰው ሆኗል ማለት ነው» ያሉት አቶ መብርሃቱ፤ የውጭ አገር ዜግነት ያለው ሰው፤ በሌላ አገር ውስጥ የፖለቲካ ተሳትፎ ማድረግ እንዳማይችል ጠቁመዋል። በተጨማሪም ሀገሪቷ በምታካሂደው ምርጫ መሳተፍ የሚችለው በታዛቢነት ብቻ መሆኑን ዓለምአቀፍ ህጎች እንደሚደነግጉም አመልክተዋል። ስለዚህም በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ገብቶ እንደፈለገው የማድረግ መብቱ በህጉ መሰረት የተዘጋ መሆኑን ገልፀዋል።

አቶ መብርሃቱ እንደገለጹት፤ ማንኛውም ፓርቲ ከውጭ አገር ዜጋ ወይም ከነዚህ ምንጮች የተገኘ ገንዘብ ወይም ንብረት ከተጠቀመ በህጉ ይወረሳል፤ ፓርቲውም በህግ ይጠየቃል። ከዚህ ጋር በተያያዘ ለዜጎች ብቻ በተፈቀደ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ወይም ስራ ላይ የተሳተፈ የውጭ አገር ዜጋ የምርጫን ሂደት ያወከ እንደሆነ በወንጀለኛ መቅጫ ህግ መሠረት ይጠየቃል። ኢትዮጵያም ለዚህ ህግ ከማውጣቷም በላይ እርምጃዎችን መውሰዷንም ተናግረዋል።

የህግ ባለሙያው አቶ ዘፋንያ ዓለሙ፤ በኢፌዴሪ ህገ መንግስት ላይ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ በመሰለው መልክ ህጋዊ በሆነ አግባብ መደራጀት ይችላል እንደሚል ጠቅሰው፤ «የፖለቲካ ፓርቲዎች በሚደራጁበት ወቅት ደግሞ ኢትዮጵያዊ መሆን እንዳለባቸው ያመለክታል» ብለዋል። አንዳንድ የፖለቲካ ፓርቲዎች «ገንዘቡን የሚያመጡት ከዚህ ነው፣ ከዛ ነው» የሚባል ነገር እንደሚሰማ አመል ክተው፤ ነገር ግን በአገሪቷ ህግ መሰረት የዚህ ዓይነቱ ድርጊት ሙሉ ለሙሉ ስህተትና የማይቻል መሆኑን አረጋግጠዋል።

የአንድን አገር የአስተዳደር ስልጣን የመወሰን ዕድል የዜጎች ብቻ ነው። ስለዚህም የውጭ አገር ዜግነት ያላቸው ማናቸውም ሰዎች በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ መግባት፣ የፖለቲካ ድርጅት ማቋቋምም ሆነ በተቋቋመ ፓርቲ ውስጥ አባል የመሆን፣ እንዲሁም መምረጥም ሆነ መመረጥ አይችሉም። ፓርቲዎቹ ከሌላ የውጭ አገር ዜጋ የሚያገኙትን ገንዘብ መጠቀምም ሙሉ ለሙሉ አይቻልም። ይህም በፖለቲካ ፓርቲ ምዝገባ አዋጅ ቁጥር 573/2000 ላይ በግልፅ መቀመጡንም የህግ ባለሙያው ጠቅሰዋል።

የማይገባቸውን ድርጊት ፈፅመው ቢገኙ ቅጣት እንዳለው የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ አዋጅ በግልጽ መደንገጉን ነው የተናገሩት። ቦርዱም አንድ የፖለቲካ ፓርቲ ሊመዘገብ ሲመጣ የውጭ አገር ዜጋ ያለበት ከሆነ እንደ ማይመዘግብና እነደሚቆጣጠር ተናግረዋል።

የህግ ባለሙያው «ትውልደ ኢትዮጵያዊ መሆን በኢንቨስመንት፣ በልማትና በሌሎች ላይ ለመሳተፍ ካልሆነ በስተቀር የፖለቲካ ተሳትፎ የማድረግ መብት አያስገኝም፤ ትውልደ ኢትዮጵያውያኑ በኢትዮጵያ ልማት ውስጥ እንዲሳተፉ እንጂ የፖለቲካው ጉዳይ አይመለከታቸውም» ብለዋል።
ምንጭ: ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment