Monday, January 19, 2015

የከተራ በዓል በድምቀት ተከብሮ ዋለ

(ጥር 11/2007, (አዲስ አበባ ))-- የእየሱስ ክርስቶስ የበዓለ ጥምቀት ዋዜማ የከተራ በዓል በመላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ በድምቀት ተከብሮ ዋለ።

Ethiopian Timket (Ethiopian Epiphany) Festival


በዓሉ በተለይ እዚህ በአዲስ አበባ በሚገኘው ጃንሜዳ የተከበረው በሺህዎች የሚቆጠሩ የእምነቱ ተከታዮች፣የውጭ አገራት ቱሪስቶች፣ አምባሳደሮችና ሌሎችም እንግዶች በተገኙበት ነበር። ታቦታቱ ከየአድባራቱ ሲነሱ ብዑዓን ጳጳሳት፣የሰንበት ተማሪዎች፣ጥንግ ድርብ የለበሱ መዘምራን፣ ልብሰ ተክህኖ የለበሱ ዲያቆናት ቀሳውስት፣

በሺህዎች የሚቆጠሩ ምዕመናን፣የውጭ ዜጎች በዓሉ ወደሚከበርበት ሥፍራ በታላቅ ሃይማኖታዊ  ስርዓት አምርተዋል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ብጹህ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስ  ከብጹዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጋር በመሆን ወደ ባህረ ጥምቀቱ ሥፍራ ሲደርሱ በበዓሉ አከባበር ላይ በነበሩ ምእመናን ዘንድ ደማቅ አቀባበል ተደርጎላቸዋል። ብጹእነታቸው ቃለ-ምእዳንና ቡራኬ ከሰጡ በኋላ ታቦታቱ ለማደሪያ ወደ ተዘጋጀላቸው ድንኳኖቻቸው ገብተዋል።

"ኅብረተሰቡ በዓሉን ማከበር ያለበት አንድነቱን፣ አገር ወዳድነቱንና በኅብረትና በፍቅር አብሮ የመኖር ባህሉን በሚያሳይ መልኩ ሊሆን ይገባል"  ሲሉ ፓትርያርኩ ገልጸዋል። ኅብረተሰቡም የዓሉን ትወፊት በመጠበቀ መልኩ እንዲከብር ያሳሰቡት አቡነ ማቲያስ ለወደፊትም በዓሉን፣ ባህሉንና አንድነቱን እንዳስተበቀ መቀጠል እንዳለበት ጥሪ አቅርበዋል።

ይህ ከከተራ ጀምሮ ለሶስት ተከታታይ ቀናት በደማቅ የሚከበረው በዓል በኢትዮጵያ ለየት ያለና ማራኪ በመሆኑ አገሪቱ በሌሎች አገሮች ጎልታ እንድትታይና ሌሎችም እንዲጎበኟት ያደረገ መሆኑንም አብራርተዋል።  

በነገው እለት ከንጋቱ 12 ሰዓት ጀምሮ የጥምቀት በዓል ይከበራል። በአዲስ አበባ 16 የተለያዩ ቦታዎች የሚያድሩት ታቦታቱ በነገው እለት ከጥቂቱ በስተቀር  በመጡበት አኳኋን ወደየአጥቢያቸው ይመለሳሉ። ምንጭ:  ኢዜአ

No comments:

Post a Comment