Sunday, November 16, 2014

በህዝብ ለህዝብ ትስስሩ፤ በሁለት አገር የሚኖር አንድ ህዝብ መፍጠር ይቻላል

(Nov 15, 2014, (አዲስ አበባ))-- «ለሰው ልጆች ሠላም፣ ለሰው ልጆች ፍቅር ከአጽናፍ እስከ አጽናፍ፣ለሰላም እንዘምር.....»  የሚለው ዜማ በአዳራሹ ያስተጋባል።ታዳሚውም በአንድ ልብና ሃሳብ ያለ በሚመስል ጥልቅ ተመስጦ ያዳምጣል።ጉዳዩን አውቆ በቦታው የተገኘ ካልሆነ በስተቀር በአዳራሹ የተገኘ እንግዳ ሰው ቢኖር አዳራሹን የሞሉት ተሰብሳቢዎች ከየት መሆናቸውን ካልተናገሩ በቀር በዕይታ አይለዩም።አንድ ዓይነት ቋንቋ ይናገራሉ።ተመሳሳይ የቆዳ ቀለምና መልክም አላቸው።

የኢትዮጵያና ኤርትራ ወንድማማች ህዝቦች ባህል፣ቋንቋ፣ሃይማኖትና ታሪክ ያስተሳሰራቸው ከመሆኑ ባሻገር በጋብቻ የተሳሰሩና የተዋለዱ መሆናቸው ታፍኖ ሊቀር የማይችል እውነት መሆኑን ከትናንት በስቲያ በጊዮን ሆቴል በተካሄደው ሁለተኛው ዙር የኢትዮጵያና ኤርትራ ህዝቦች የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት ለሰላም ኮንፍረንስ የተሳተፉ የሁለቱ አገሮች ዜጎች ይገልጻሉ።ይህን የማይሻር አንድነት ወደነበረበት ለመመለስና ወንድማማች ህዝቦች በሁለት አገራት እያሉ በሰላምና ፍቅር እንዲኖሩ ህዝቦች ከፖለቲካዊ ይዘት በጸዳ መንገድ የድርሻቸውን ሊወጡ እንደሚገባም ይናገራሉ።

ኤርትራዊው አርቲስት ርዕሶም ገብረጊዮርጊስ በኢትዮጵያና ኤርትራ ህዝቦች መካከል አንድነት ተፈጥሮ ሰላም እንዲነግስ ያለውን እምነት የገለጸበት፣ ምኞቱም እውን እንዲሆን ህዝቦችና ሁሉም ባለድርሻዎች ለዚሁ ዓላማ የድርሻቸውን እንዲያ በረክቱ የጠየቀበት «ሠላም» በሚል ርዕስ ያዘጋጀውና በስብሰባው የተመረቀው ሙዚቃም የታዳሚዎቹን ቀልብ በበለጠ የገዛ ሆኗል።

ለህዝቦች ሰላምን ለመስበክ የጥበብ ሥራውን ለሰላምና ልማት መስፈን በተለያዩ አገራት በማቅረብ አሻራውን እያኖረ የሚገኘው አርቲስት ርዕሶም፤ጥበብ እንኳን የምታድገውና የምትደመጠው በህዝቦች መካከል ሰላምና ፍቅር ሲኖር መሆኑን ነው የገለጸው።ለኢትዮጵያና ኤርትራ ህዝቦች በሰላምና በፍቅር መኖር በጥበብ ዘርፍ የተሰማሩ ባለሙያዎች የድርሻቸውን እንዲያበረክቱም ጠይቋል።

የኢንተር አፍሪካ ግሩፕ ዋና ሥራ አስኪያጅ ኢትዮጵያዊው አቶ ታምራት ከበደ፤በፖለቲካው ጉዳይ ከመለያየታቸው በፊት እስከ ነጻነት ትግል ወቅት በሁለቱ አገሮች ህዝቦች መካከል ጠንካራ አንድነት እንደነበር ያስታውሳሉ።የነዚህ አገራት ትስስር ደግሞ ከማህበራዊ አንድነቱ ባለፈም የመልክዓ ምድራዊ ሁኔታውም አጋዥ መሆኑን ይጠቁማሉ።በመሆኑም እነዚህ በሁለት አገር የሚኖሩ ህዝቦች አንድ የመሆን ጊዜያቸው ሊረዝም ቢችልም በሁለት አገር እየኖሩ አንድ መሆናቸው ግን እውን መሆኑ እንደማይቀር የቻይናን ታሪክ በማውሳት ያላቸውን እምነት ይገልጻሉ።ለዚህም ከመንግሥት ይልቅ የህዝብ ለህዝብ ግንኙነቱ ትልቅ ድርሻ ያለው በመሆኑ የበለጠ እንዲሰሩበት ጥሪ ያስተላልፋሉ።

የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪ ኤርትራዊው ክንፈ ሚካኤል በበኩሉ፤ከተቋረጠ ዓመታትን ባስቆጠረው የሁለቱ አገራት ግንኙነት ሳቢያ ስለሁለቱ ሀገሮች ህዝቦች አንድነት ጥልቅ ታሪካዊ ዳራ እንደሌለው ገልጾ፣ በስደተኝነት ቆይታው ግን ብዙ የተገነዘበው እንዳለ ይገልጻል።እነ ክንፈ ከስደተኛ ጣቢያዎች ወደ ዩኒቨርሲቲው ሲገቡ የዩኒቨርሲቲ መምህራን ሳይቀሩ የፍቅር አቀባበል አድርገውላቸዋል፤ልምዳቸውን አካፍለዋቸዋል።ይህ ሁሉ የሁለቱ አገራት ህዝቦች አንድነት ታሪክ የማይሽረው መሆኑን እንደሚያሳይ ነው የገለጸው።

ተማሪ ክንፈ ሚካኤል በቆይታውም በርካታ ኢትዮጵያዊ ጓደኞች አፍርቷል።በቤታቸውም ተጓብዟል። እርሱም ዕድሉ አይኑረው እንጂ እንደ ኢትዮጵያውያን ጓደኞቹ ሁሉ እርሱም የእናቱን ማጀት የዶሮ ወጥ ለጓደኞቹ የመጋበዝ ጽኑ ፍላጎት አለው።ታድያ ይህ ምኞቱ እውን እንዲሆንና እርስ በርስ የተሳሰሩ ህዝቦች በሰላምና ፍቅር አብረው እንዲኖሩ ህዝቡ ትልቅ ድርሻ እንዳለው ነው የጠቆመው።በተለይም ወጣቱ ትውልድ የተዛባ ታሪክን ይዞ በጥላቻ እንዳያድግ በማድረግና ለህዝቦቹ አንድነት እንዲሰራ የህዝቡን ታላቅ ሥራ ይጠይቃል።

ሌላው ኤርትራዊ ወጣት ቢኒያም አፈወርቂ በበኩሉ እንደሚናገረው፤ሰፊው የኤርትራ ህዝብ አይደለም ኢትዮጵያውያን ወገኖቹን ማንኛውንም ህዝብ የሚወድና የሚያከብር ነው።ስርዓቱ አፍኖ የያዘው ባይሆንና እንደ ኢትዮጵያውያን ወገኖቹ በነጻነት መንቀሳቀስ ቢችል ይህን ታላቅ ዓላማ ከግብ ለማድረስ ሁሌም ያስባል።በመሆኑም የኢትዮጵያ ህዝቦችና የሲቪል ማህበራት ሁሉ ከአቻ ማህበራትና ኤርትራዊ ወገኖቻቸው ጎን በመቆም ሊሰሩና ሊደግፏቸው እንደሚገባ ያስገነዝባል።

በኢትዮጵያ የሰላምና የልማት ዓለምአቀፍ ኢንስቲትዩት የህዝባዊ ኮንፍረንስ አዘጋጅ ኮሚቴ አባላት አቶ አበበ አይነቴና አቶ ፀጋልኡል ወልደኪዳን እንደሚናገሩት፤የኮንፍረንሱ ዓላማ የየትኛውንም ወገን የመንግሥት አካል ማውገዝና መተቸት ሳይሆን፣የሁለቱ አገር ህዝቦች በአንድ መድረክ ተገናኝተው በቀጣይ ግንኙነታቸው ዙሪያ ከፖለቲካዊ መስመር ውጪ ሃሳባቸውን እንዲያራምዱ ማስቻል ነው።በዚህ ረገድም ሁለቱ ህዝቦች ተገናኝተው ቀጣይ በሰላምና በፍቅር ሊኖሩ ስለሚችሉበት ሁኔታ በግልጽ መነጋገር ችለዋል።ሰላምም ሆነ ጦርነት የሌለበትን ግንኙነት በመቀየር ሰላማዊና ወንድማዊ አንድነትን መፍጠር እንደሚፈልጉም አመልክተዋል።ሌሎች መድረኮችን በመፍጠርም ውይይቱ ተጠናክሮ የሚቀጥል ይሆናል።

የኢንስቲትዩቱ ምክትል ኤክስኪዩቲቭ ዳይሬክተር አቶ ሞገስ ተክለሚካኤል እንደሚናገሩት፤የሁለቱ አገሮች ህዝቦች በተለያየ መልኩ የተሳሰሩ ናቸው።ኮንፍረንሱም ይህንን ትስስርም ወደነበረበት ለመመለስ የነጻ ህዝቦች የህዝብ ለህዝብ የሰላምና የፍቅር አጀንዳ ይዞ የሚከናወን እንደመሆኑ በሁለት አገራት የሚኖር አንድ ህዝብን ለመፍጠር ያስችላል።በመሆኑም በተለያዩ አገራት ከተከሰቱ ግጭቶች በመማርም የህዝቦችን ማህበራዊ አንድነት ለመፍጠር ልምድ በመውሰድ ጊዜ የፈጠረው ግጭት ታሪካዊውን ትስስር እንዳይሸፍነው መስራትና አንድ መሆን ይጠይቃል። ለዚህም በኢትዮጵያ ያሉም ይሁን በሌሎች አገራት ያሉ ኤርትራውያን ወገኖች ባላቸው ነጻነት ከኢትዮጵያ ወገኖቻቸው ጋር ሰላምና ፍቅርን እንዲያጸኑ በመስራት፣ወደተሻለ ደረጃ በማሳደግ መጀመር ይገባል።

የኮንፍረንሱ ተሳታፊዎች በቅኝ ግዛት ወቅት እንኳን ያልተቋረጠውን የኢትዮጵያና የኤርትራ ህዝቦች የጋራ ጥቅምና ትስስር በጋራ ለማስቀጠል ተመሳሳይ ህዝባዊ ኮንፍረንሶችን ለማዘጋጀትና የሁለቱን አገራት ህዝቦች ጎድቶ የቆየውን አመለካከት ለመቀየር የሚያስችል ሥራ ከሁሉም ባለድርሻ የሚጠበቅ በመሆኑ ይህንኑ ለመወጣት ቁርጠኛ መሆናቸውን የሚያመለክት ባለ አራት ነጥብ የአቋም መግለጫ አሰምተዋል።
ምንጭ: ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment