Wednesday, November 12, 2014

ለጋማ ጋማማ አህያም ጋማ አላት፤ አያስጥልም እንጂ ጅብ ሲዘነጥላት

(Nov 11, 2014, (አዲስ አበባ))--በጅቦች መንደር ነው አሉ። ሦስት አህዮች በጠፍ ጨረቃ ሰፊ መስክ ላይ ተሰማርተው ሳር እየጋጡ ዓለማቸውን ይቀጫሉ። በዚህ መሀል ሦስት ጅቦች የሚበላ ፍለጋ ሲዘዋወሩ አህዮቹን ይመለከቷቸዋል። በአህዮቹ ድፍረት የተገረሙት ጅቦቹም «እነዚህ አህዮች እንዴት ቢጠግቡ እንዴትስ ቢንቁን ነው በእኛ ሰዓት፣ በእኛ ግዛት እንደዚህ ተዝናንተው ሳር የሚግጡት?» ሲሉ እርስ በርስ ይጠያየቃሉ። አውጥተው አውርደውም ለምን ችሎት ተቀምጠን አንፈርድባቸውም በማለት ይወስናሉ። አህዮቹም በየተራ ወደ ጅቦቹ እየቀረቡ ጥያቄ ይቀርብላቸው ጀመር፤

የመጀመሪያዋ አህያ ቀረበች፤
«እመት አህያ እንደው ለመሆኑ ማንን ብትተማመኚ ነው በዚህ ሌሊት በእኛ ግዛት ያላንዳች ከልካይ ሳር የምትግጭው?» ተብላ ተጠየቀች። አህይትም ሳትፈራ ቅምም ሳይላት «ፈጣሪዬን ተማምኜ ነው፡፡ በእኔ ላይ ግፍ የሚሠራ ካለ የፈጠረኝ ዝም አይለውም፤ መዓት ያወርድበታል» ስትል ለጅቦቹ መልሷን ሰጠች። ፍርዱን በኋላ ተብላ ተራውን ለሁለተኛው አህያ ለቅቃ ዞር ብላ ተቀመጠች።

ለሁለተኛዋ አህያም ተመሳሳይ ጥያቄ ቀረበላት። እርሷም በተመሳሳይ ሳትደናገጥ «አሳዳሪዬን ተማምኜ ነው፡፡ በእኔ ላይ ጥቃት የሚያደርስ ካለ አሳዳሪዬ ዝም አይለውም፤ ይበቀልልኛል» በማለት ምላሿን ሰጠች። እርሷም ፍርዱን እንድትጠብቅ ተነግሯት ለሦስተኛዋ አህያ ስፍራውን ለቀቀች።

ጅቦቹ ሦስተኛዋን አህያ አስቀርበው «አንቺስ ማንን ብትተማመኚ ነው በዚህ ጠፍ ጨረቃ ይህን ዓይነት ድፍረት ይህንን ዓይነትም መዝናናት?» ሲሉ በግርምት እንደተሞሉ ጠየቋት። ይህችኛዋ አህያም ትንሽ አሰብ አድርጋ፤ «አንደኛ እናንተን የአካባቢውን ንጉሶች ሁለተኛም ጋማዬን ተማምኜ» ስትል ቃሏን ሰጠች። በመልሷ ፈገግ ያሉት ጅቦቹም ፍርዷን እንድትጠብቅ እስከዚያው ከመሰሎቿ ጋር እንድትቀመጥ አዝዘው ለብቻቸው መምከር ጀመሩ።

ጅቦቹ ማንን መብላት እንዳለባቸው አወጡ አወረዱ። «የመጀመሪያዋን ብንበላት ፈጣሪ አይለቀንም። ሁለተኛዋን ብንበላትም አሳዳሪዋ ይበቀለናል። እኛንና ጋማዋን የተማመነችውን አህያ ብንብላት ማንም አይነካንም፤ እስኪ ጋማዋም ያስጥላት እንደሆነ እንይ?» ሲሉ ተስማሙ። ሮጠው በመሄድም ሦስተኛዋ አህያ ላይ ሰፈሩባት። ዘነጣጥለውም ረሃባቸውን አስታገሱባት አሉ።

እንዲህ እንደተረቱ ሁሉ በመካከላችንም ብዙ አህዮች ብዙም ጅቦች እንዳሉ ልብ ብለው አይተው ይሆን? የእርስዎን ምላሽ ለእርስዎ ልተወውና የእኔን ትዝብት ልንገርዎት። ሰሞኑን ከወደ ተባበሩት መንግሥታት የተሰማ ዜና አለ። የኤርትራ መንግሥት በኢትዮጵያ መንግሥት አሸባሪ ተብለው ከተሰየሙ ድርጅቶች ጋር ቃል ኪዳን ማሰሩንና ለዚህም ሥራ በዝቶበት ሽርጉድ ሲል መክረሙን ድርጅቱ ይፋ ካደረገው መረጃ አንብበናል። ምስራቅ አፍሪካ ጭር ሲል የማይወደው ሻዕቢያ የአልቃይዳ ክንፍ ከሆነው አልሸባብ፣ ራሱን የኦጋዴን ነጻ አውጪ ግንባር (ኦብነግ) ብሎ ከሚጠራው አሸባሪ ድርጅት ጋር ብቻ ሳይሆኑ እንደ ኦነግና ግንቦት 7 የመሰሉትም የአህያዎቹንና የጅቦቹን ዓይነት ታሪክ ሊደግሙ ውል አስረዋል።

በተለይ እነዚህ ሁለቱ ( አልሸባብና ኦብነግ) በቀጣናው የሽብር ንጉስ በሆነው ጅቡ የኤርትራ መንግሥት ግዛት ስር የወዳደቀ ትርፍራፊ ሊቃርሙ መጓዛቸው እርሱንም ተማምነው መኖራቸው ብዙም አይገርመንም። ምክንያቱም መጨረሻቸው እርስ በርስ መዘነጣጠል እንደሚሆን እንኳንስ እኛ እነሱም አሳምረው ያውቁታል። የማይተማመኑ ባልንጀራሞች በየወንዙ ዳር መማማላቸውም ደንብ ነው። አሁንም የሆነው ይሄው ነው። በሶማሊያ የነበረውን ግዛት ሁሉ እየተነጠቀ መፈናፈኛ ያጣው አልሸባብና በኢትዮጵያ የመከላከያ ሠራዊት አከርካሪው ተሰብሮ የተባረረው ሽርፍራፊ የኦብነግ ኃይሎች የኤርትራን መንግሥት ተማምነው ከእርሱ ጋር ውል ማሰራቸው የመጨ ረሻቸው መጀመሪያ ላይ መድረሳቸውን መረዳት አላቃተንም።

የድርጅቱ መግለጫ የኤርትራ መንግሥት እ.አ.አ በ1907 የተፈረመውን ዓለም አቀፍ ስምምነት ወደ ጎን በመተው ለኦብነግ የትጥቅና የገንዘብ ድጋፍ እያደረገ ይገኛል ሲል ይከሳል። በዚህ ድጋፍ የልብ ልብ ያገኘው አሸባሪው የኦጋዴን ነጻ አውጪ ግንባርም አቅጣጫውን በመቀየር ወደ ሞቃዲሾ በማቅናት ከአልሸባብ ጋር የሎጅስቲክ ስምምነት አድርጓል። ጌታውንና ጅቡን የኤርትራ መንግሥት ተማምኖ።

እንደሚታወቀው በእ.አ.አ በ2012 አብዛኛው የኦጋዴን ነጻ አውጪ ግንባር ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር የሰላም ድርድር በማድረግ ትጥቅ ፈትቶ በሰላም ወደ ክልሉ ተቀላቅሏል። ነገር ግን ይሄንን መንገድ ያልፈለጉ ጥቂት የቡድኑ አባላት እንደገና በመሰባሰብ ወደ እኩይ ተግባራቸው ተመልሰዋል። ይህ ቡድን ያለፈቃዳችን ያለ እኛም ስምምነት በቅኝ ግዛት ውስጥ ነን ብሎ የሚያምን ነው። ልብ ይበሉ ኦብነጎች እያሉ ያሉት የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል በቅኝ ግዛት ስር ነው እንደ ማለት ነው። ይህች አስተሳሰብ ደግሞ የማን እንደሆነች በደንብ ትታወቃለች። የጌታቸው የጅቡ ይቅርታ የኤርትራ መንግሥት ፀረ ኢትዮጵያ አቋም ናት። ይሄው የምስራቅ አፍሪካ ሰላም የሚያመው የኤርትራው ሰውዬ የሚመራው መንግሥት እነዚህን ሲበሉ የላኳቸውን ጀሌዎቹን እያሰለጠነ እያሰየጠንም ጭምር የረጅም ጊዜ ህልሙን ያሳኩለት ዘንድ ላይ ታች ማለቱን ቀጥሏል።

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የኤርትራው ፕሬዚዳንት አማካሪ በየማነ ገብረአብ እና በስለላ ክፍል ዋና ኃላፊው አብረሃ ካሳ አስተባባሪነት በተደረገ ኮንፈረንስ የኡጋዴን ነጻ አውጪ ግንባር መቀመጫውን ወደ ሶማሊያ ሞቃዲሾ እንዲያደርግ ተስማምተዋል። ለዚህ የስፍራ ቅያሬም የተሰጠው ምክንያት በሞቃዲሾ ያለውን ያልሰከነ የጸጥታ ሁኔታ በመጠቀም ድርጅቱን መሳሪያ ለማስታጠቅና መልሶ ወደ ኦጋዴን አካባቢ ለማሰማራት የሚል ነው። ይህ የኢሳያስ መንግሥት ቁማር የት እንደሚያደርሳቸው ወደፊት የሚታይ ቢሆንም ከወዲሁ መናገር የሚቻለው ግን የኦብነግ እጣ ፋንታ ጋማዋንና ጅቦችን እንደተማመነችው አህያ መሆኑ አይቀርም።

የኢትዮጵያ መንግሥት እጅግ ጠንካራ የሆነ የደህንነት መረብ እንዳለው ወዳጅም ብቻ ሳይሆን ጠላት የሚያውቀው የአደባባይ ምስጢር ነው። ታዲያ ኦብነግ ይሄንን አጥቶት ይሆን የቀቢጸ ተስፋ ተግባር እየፈጸመ ያለው? አይደለም። ጅቦቹን እንደተማመነችዋ አህያ ሆኖ እንጂ። ይሄ አሸባሪ ድርጅት ከጌታው የኤርትራ መንግሥትም በላይ የመከላከያ ሠራዊታችንን የፈረጠመ እጅ በተደጋጋሚ የቀመሰው ነውና ኦጋዴን ብሎም ኢትዮጵያ ሱሚ መሆናቸውን ጠንቅቆ ያውቃል።

ሪፖርቱ የኤርትራ መንግሥት ለኦብነግ የገንዘብ ድጋፍ እያደረገ ስለመሆኑ በደፈናው ሳይሆን አብነት በመጥቀስ ነው የጥፋት አባትና ልጅ መሆናቸውን ያጋለጠው። የኢሳያስ መንግሥት በተባበሩት አረብ ኤሜሬትስ ዱባይ የሚገኝን ባንክ በመጠቀም ለኦጋዴን ነጻ አውጪ ግንባር ገንዘብ አስተላልፏል። የአስመራ ሰዎች ዱባይ ወደ ሚገኝ የአሸባሪው ድርጅት አካውንት ታዋካል የሚባል የሃዋላ አገልግሎትን በመጠቀም ጠቀም ያለ ገንዘብ አስገብተዋል። ይህ የገንዘብ አካውንት ደግሞ ነዋሪነቱ አውስትራሊያ በሆነ የአሸባሪው ድርጅት ምክትል ሊቀመንበር ሞሀመድ ኢስማኤል ስም የሚንቀሳቀስ ነው። ይህ ገንዘብ በግለሰቡ ከወጣ በኋላ ባልታወቀ ሌላ ሃዋላ አማካኝነት ለአሸባሪዎቹ እንዲደርስ ተደርጓል። ሽብርተኝነትን በገንዘብ የመደገፍ ድርጊት ደግሞ በኢትዮጵያም ብቻ ሳይሆን በዓለም አቀፍ ህግ የሚያስጠይቅ እኩይ ተግባር ነው።

የኤርትራ መንግሥት የዚህን ዓይነት የወንበዴ ሥራ የሚሰራው ለኢትዮጵያ ካለው ጥልቅ ጥላቻ በመነሳት ነው። አሸባሪው ድርጅት ኦብነግም ሆነ አልሸባብ ከኤርትራ ህዝብ ጋር ምንም የሚያመሳስልም ብቻ ሳይሆን አንድ ሊያደርግ የሚችል ቁመናና ዓላማ የላቸውም። ነገር ግን የጠላቴ ጠላት ለእኔ ወዳጄ ነው በሚለው የዜሮ ድምር ፖለቲካ ቀመር እነዚህ ጌታቸውንና ጋማቸውን የተማመኑ አሸባሪ ድርጅቶች ጣታቸውን በኢትዮጵያ ላይ ቀስረዋል። በዚህ ድርጊታቸውም ከተጠያቂነት እንደማያመልጡ እኛም ብቻ ሳንሆን የዓለም መንግሥታት አሳስበዋል።

በተለይ ደግሞ በሪፖርቱ ላይ የተጠቀሱት የኤርትራ መንግሥት ከፍተኛ ባለስልጣናት ከዚህ ሁሉ ሴራ ጀርባ ያሉ መሆናቸው ታውቋል። የተባበሩት መንግሥታት ሪፖርት ኮሎኔል ተወልደ ሀብቴ፣ ኮሎኔል ሙሳ እና ኮሎኔል ሀጎስ የተባሉ ከፍተኛ የኤርትራ መንግሥት ወታደራዊ ባለስልጣኖች ለኦጋዴን ነጻ አውጪ ግንባር ባህር ተሻግሮ መሄድ ተጠያቂ ናቸው ይላል። እነዚህ ወታደራዊ ባለስልጣኖች በተጨማሪ ከኤርትራ መንግሥት ድጋፍ ለሚያገኙ ታጣቂዎች ክትትል የሚያደርገውና የፕሬዚዳንቱ የቅርብ ሰው የሆነው ኮሎኔል ተስፋልደት ሀብተሥላሴም እጁ እንዳለበት ይገልጻል።

ይኸው ሪፖርት በቀቢጸ ተስፋ እየተንቀሳቀሰ ያለው የኦጋዴን ነጻ አውጪ ግንባር በአሁኑ ወቅት መቀመጫውን በሰሜናዊ ሞቃዲሾ ጋልካሲዮ በተባለ አካባቢ አድርጓል። ይህ ቦታም የተመረጠው ወደ ኢትዮጵያ እንደልባቸው ለመግባትና ለመውጣት ወታደሮችንም ለማሰልጠን መሳሪያም ወደ ኢትዮጵያ ለማስገባት ይመቸናል ብለው እንደሆነ ሪፖርቱ እማኞችን በመጥቀስ ያብራራል። በተጨማሪም መሳሪያ እንደልባቸው ለመሸመት አካባቢው ምቹ መሆኑ ተገልጿል።

የኢትዮጵያ መንግሥት የደህንነት መረብና የመከላከያ ሠራዊቱም የመዘናጋት ባህሪ ቢኖራቸው ኖሮ ፍርሃት ይሰማን ይሆን ይሆናል። እንደመታደል ሆኖ ግን የኢትዮጵያ ደህንነት መዋቅርና የመከላከያ ሠራዊት ፍጹም ጠንካራና በጅቦችና ጅቦችን በተማመኑ አህዮች የሚሰበር አይደለም። ስለዚህም የእኛ መልዕክት ዛሬም እንደቀደመው ጊዜ ሁሉ ተመሳሳይ ነው፤ « አልሆነ ልሽም አንቺ ጋለሞታ ቂጣሽን በልተሽ ወደ መኝታ» የሚል። አበቃሁ!
ምንጭ: ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment