Wednesday, November 06, 2013

ጉዞው እንዲቋረጥ የተወሰነው ለዜጎች ደህንነት ሲባል ነው

(Nov 06, 2013, (አዲስ አበባ))--የኢትዮጵያ መንግሥት በኮንትራት ወደ ተለያዩ የዓረብ ሀገሮች ለጉልበት ሥራ የሚደረገው ጉዞ ለጊዜው እንዲቆም ያደረገው ዜጎች እየደረሰባቸው ያለውን ሰብዓዊና ሥነልቦናዊ ጉዳት ለማስቀረት መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ትናንት በሚኒስቴሩ አዳራሸ መግሥት በተወሰኑ ዓረብ አገሮች ለጉልበት ሥራ ዜጎች የሚያደርጉት ጉዞ ላልተወሰነ ጊዜ እንዲቋረጥ ስለመደረጉ፣ ኢትዮጵያ በጎረቤት ሀገሮች የሰላም ተልዕኮዋን ስለማጠናከሯና በኬኒያ መሪዎች ላይ ዓለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት የመሰረተውን ክስና ተያያዥ ጉዳዮች በተመለከተ ለጋዜጠኞች ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡

አምባሳደር ዲና ሙፍቲ በማብራሪያቸው ለሥራ ወደ ተለያዩ ሀገሮች የሚደረገው ጉዞ ዜጎችን ለሰብዓዊ፣ ለሥነልቦናዊ፣ አካላዊ ጉዳትና ለሞት አደጋ ከመዳረጉ በተጨማሪ በሀገር ልማትም ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ አሳድሯል፡፡ በተለይም ወደ መካከለኛው ምሥራቅ የሚሄዱ ዜጎች አብዛኞቹ ከገጠሪቱ የኢትዮጵያ ክፍል ሊሠራ የሚችል ትኩስ ኃይል መሆኑን በማስታወስ፤ ይህ ኃይል መሄዱ በእርሻ የሥራ እንቅስቃሴው ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ እያሳደረ መሆኑን አመልክተዋል፡፡ በዚህ የተነሳ የሚከሰተው ማህበራዊ ቀውስ ቤተሰብን በከፍተኛ ሁኔታ እየጎዳ መሆኑንም በተደጋጋሚ መታየቱን ገልጸዋል፡፡

ዜጎች «የተሻለ ሥራ ፍለጋ» በሚል ሰበብ በሚያደርጉት ጉዞ በመንገድና ለሥራ በሄዱበት ሀገር ጭምር ለአደጋና ስቃይ እየተጋለጡ መሆናቸውንም አመልክተዋል። በሀገሮቹ የሚገኙ ቆንስላ ጽሕፈት ቤቶችና ኤምባሲዎችም የእነዚህን ዜጎች ችግር ለመፍታት ሰፊ ጊዜ እየወሰዱ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡ መንግሥትም እነዚህን ተደራራቢ ችግሮች በተለይም በዜጎች ላይ የሚደርሰውን ስቃይ አስከፊነት ግምት ውስጥ በማስገባት ሁኔታዎች እስኪመቻቹ ድረስ ጉዞው እንዲቋረጥ ማድረጉን አመልክተዋል፡፡ ሌሎች ሀገሮች እንደሚያደርጉት ዜጎች በሥልጠና አቅም እስኪፈጥሩና ሙሉ ዋስትና እስኪያገኙ በይበልጥ ወደ ሊባኖስ፣ ኳታር፣ ሳውዲ ዓረቢያ፣ ኩዌት፣ የመን፣ ሱዳንና ደቡብ አፍሪካ በኮንትራት ለጉልበት ሥራ የሚደረገው ጉዞ ለጊዜው እንዲቆም ውሳኔ መተላለፉን አስታውሰዋል፡፡

ኢትዮጵያ በጎረቤት ሀገሮች የሠላም ተልዕኮዋን በተጠናከረ ዲፕሎማሲያዊ መስክ መቀጠሏን ያስታወሱት አምባሰደሩ፤ በሶማሊያ ፌዴራል መንግሥትና በጁባ ግዛት መካከል ከአንድ ወር በፊት የተደረገው የሰላም ስምምነት ይበልጥ ለማጠናከር በአሁኑ ወቅት በአዲስ አበባ በውይይት ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ውይይቱንም የኢትዮጵያ ተወካይ ባለበት የሶማሊያ የፌዴራል መንግሥትና የጁባ አስተዳደር ልዑካን በጥሩ ሁኔታ በማካሄድ ላይ እንደሚገኙ አመልክተው፤ በውጤታማነት ይጠናቀቃል ተብሎ እንደሚጠበቅም አምባሳደሩ ገልጸዋል፡፡

አምባሳደር ዲና በኬኒያ የተፈጸመው የሽብር ጥቃት ኢትዮጵያን አያሰጋትም ወይ? ለሚለውና ስጋቱን ለመቀነስ ያላትን ዝግጁነት በተመለከተ ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ፤ በቀጣናው ያሉ ሀገሮች ለአልሸባብ ጥቃት የተጋለጡ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ በኢትዮጵያ በኩል «ስጋቱንና ለሽብር መሰረት የሆኑትን ችግሮች ለመቀነስ ህብረተሰቡ ተባባሪ ነው» ብለዋል፡፡ ህብረተሰቡ ልማቱ እንዳይደናቀፍ የሚከላከል ከመሆኑ በተጨማሪ የብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና የኃይማኖት እኩልነት መረጋጡም ለስጋቱ መቀነስ አስተዋጽኦ እንዳለው አመልክተዋል፡፡

በአልሸባብ ላይ የሚደረገውን ጦርነት ለማጠናከር ወደ አራት ሺ የሚሆን የሰላም ጠባቂ ተጨማሪ ጦር እንደሚያስፈልግና ከዚህ ውስጥም «ሁለት ሺ ሃምሳው አፍሪካ እንድታዋጣ ይጠበቃል» ያሉት አምባሳደር ዲና በዚህ ላይ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት እየሰራ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡

አምባሳደሩ በኬኒያ መሪዎች ላይ በዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት የቀረበውን ክስና የክሱን ለአንድ ዓመት መተላለፍ ጉዳይ አስመልክተው እንደገለጹት፤ በኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር መሪነት ከአምስት የአፍሪካ ቀጣናዎች የተውጣጡ አባላት ያሉበት ልዑካን ቡድን በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የፀጥታ ምክር ቤት አባል ሀገሮች ጋር ኒውዮርክ ተገናኝተው በአንድ ድምጽ የአፍሪካን ፍላጎት ማንፀባረቃቸውን አስታወቀዋል፡፡ ይህ የአፍሪካ ሀገሮች በአንድ ጉዳይ ላይ በዚህ አይነት በዓለም አቀፍ መድረክ መቅረባቸው «የአፍሪካ ሕብረት በሌሎች ወገኖች ተቀባይነት እንዲያገኝ ያግዛል » ብለዋል፡፡ የቀረበው ቅሬታ ውጤት ወደፊት እንደሚታይም ገልጸዋል፡፡ 
ምንጭ: አዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment