Friday, September 08, 2017

እንቁጣጣሽን በአገር ባህል ቀሚስ

(Sept 08, 2017, (አዲስ አበባ))--በአዲስ ዓመት ዋዜማ ላይ እንገኛለን። በዓሉን ሞቅ ደመቅ አድርጎ ማሳለፍ ለእኛ ለኢትዮጵያውያን የሚነገር አይደለም። በአገር ባህል ልብስ ደምቆ፣ ቄጠማ ጎዝጉዞ፣ ቡና አፍልቶ ፣እጣን አጭሶ በዓሉን በደማቅ ሁኔታ ማሳለፍ እንችልበታለን። ከሁሉም በላይ ግን በዓሉ በዓል የሚመስለው ሰዎች በአገር ባህል ልብስ ደምቀው ወዲያ ወዲህ ሲሉ ማየት ነው። አዲሱን ዓመት በአገር ልብስ ደምቃችሁ እንድትቀበሉት፤ የእንቁጣጣሽ በዓልን «እንቁጣጣሽ» መስላችሁ እንድትውሉ በጥሩ ዲዛይን የተሠሩ ልብሶች እንዳሉ ዲዛይነሮች ይገልጻሉ።

ዛሬም በዲዛይነር ብዙአየሁ ጫላ የተሠሩትን እንመልከት። በተለይ አዲሱን ዓመት ለማድመቅ ተመራጭ ናቸው ያላቸውን። ከአሠራራቸው እንጀምር፤ የባህል ቀሚሱ በመነንና በኮምታሬ ነው የሚሰራው። መነንና ኮምታሬ ተመሳሳይ ቀለምና ይዘት ቢኖራቸውም ልዩነትም አላቸው። መነን ከሆነ ሲታጠብ ይዘረዝራል፤ ኮምታሬው ግን ሲታጠብ አይዘረዝርም ይልቁንስ ሲታጠብ እያማረበት ነው የሚሄደው።

የአገር ባህል ቀሚሱ ጥበብ በጥንቃቄና በተመረጡ ሸማኔዎች ነው የሚሠራው። ከጥበቡ ጋር የሚሄድ ጥልፍም በጥንቃቄ ይጠለፍ ለታል።ብዙ ጊዜ ወርቀዘቦ፣ ቀይ፣ ቢጫና ሌሎች ቀለሞችን መጠቀም ይቻላል። በከፍተኛ ጥንቃቄ ስለሚጠለፍ በፍፁም ቀሚሱንም አያጨማድደውም።

ጥልፉም እንደየሰው ምርጫ የሚዘጋጅ ነው። ቁመቱም በደንበኛ ፍላጎት ማጠር ወይም መርዘም ይችላል። አሁን ፋሽኑ አጭር በመሆኑ በብዛት የሚመረጠው አጭሩ ነው።

በበዓል ቀን፣ በሠርግ ጥሪና በሌሎች የደስታ ቀናት ቢለበስ የሚመረጥ ቢሆንም በሥራና በአዘቦት ቀንም ሊለበስ ይችላል። ቀሚሱ በሳተን ገበር ስለሚሰፋ ከጥልፉ ቀለም ጋር የሚሄድ የገበር አማራጭ ይኖረዋል። ነጭ ሲሆን በኦርጋንዛና በነጭ ሳተርን ገበር ቢሰፋ የበለጠ ያምራል። ምክንያቱም ጨርቁ በጣም ስስ በመሆኑ ወፈር ያለ ገበር ያስፈልገዋልና።

የኢትዮጵያዊ ባህሉንና ወጉን በጠበቀ መልኩ ስለሚዘጋጅ ነጭ የአገር ባህል ቀሚስ በነጭ ገበር ቢዘጋጅ ይመረጣል። ወገቡና እጁ ላይ ያለው ጥበብ የነጠላ ጥለት ተቆርጦ ነው የሚገባው። ረጅም ቀሚስ ከሆነ ጥልፉ ሙሉ ነጠላ ነው የሚወስደው። ሲለበስ ግን በግማሽ ነጠላ ስለሚለበስ ግማሹ ነጠላ ለወገቡና ለእጁ ይሆናል። ለቤተክርስቲያን የሚፈለግ ከሆነ በሙሉ ነጠላ ይዘጋጃል።

ከወገብ በላይ ያለው በሦስት ተደራቢ ጨርቅ ነው የሚሠራው። ምክንያቱም ገበር ስለማይገባበትና ሰውነትን ማሳየት ስለማይኖርበት ደረብ ተደርጎ ይሠራል። ልብሱ ተመሳሳይ ጥበብ ጫማና ቦርሳም ይሠራለታል። ጥልፉ በፈርጥ ስለሚሠራና ጥንቃቄንም ስለሚፈልግ አንድ ሳምንት ሊፈጅ ይችላል።

ይህንን የአገር ልብስ የምትለብስ ሴት ጥለቶቹን መሠረት ባደረገ የፀጉር ቀለም ፀጉርዋን ሹርባ ብትሰራ የበለጠ ውበቷን እንደ ሚያጎላው ዲዛይነሩ ይመክራል።
ከአዲስ ዘመን

No comments:

Post a Comment