Monday, May 13, 2013

አገራችን ሙሰኞችን የመሸከም አቅም የላትም

(May 13, 2013, አዲስ አበባ))--ከኢኮኖሚያዊ ተሳትፎ ውጪ በውድድር ላይ ባልተመሠረተ አኳኋንና አሠራር እሴት ሳይጨምሩ በአቋራጭ የመክበርና የመበልፀግ አካሄድ በዋነኝነት ከመንግሥት ሥልጣን ጋር የሚያያዝና በኪራይ ሰብሳቢነት ርዕዮት ወይም አመለካከት የሚገለጽ የአብዛኛዎቹ  ታዳጊ አገሮች ነቀርሳ ነው ለማለት ይቻላል። የእዚሁ አስተሳሰብ ዋነኛ መገለጫ የሆነው ሙስናም በተመሳሳይ መልኩ በፍጥነት በማደግ ላይ በሚገኙት አገሮችና የተፈጥሮ ሀብት መሠረት ባላቸው አገሮች ላይ በእጅጉ ይበረታል።

በዓለም አቀፍ ደረጃ ከተካሄዱ የሙስና ቅኝት ጥናቶች ለመረዳት እንደሚቻለው ሙስና በማደግ ላይ የሚገኙ አገሮችን ዓመታዊ ጠቅላላ ዕድገት ከአንድ በመቶ በላይ እንዲቀንስ የማድረግ ፈርጣማ ኃይል ያለው ነው።

በኢንቨስትመንት ረገድም ከበለፀጉት አገሮች ጋር ሲነፃፀር ሙስና በተንሰራፋባቸው አገሮች የመስኩ ዕድገት በአምስት በመቶ ያህል ቅናሽ እንደሚያሳይ ጥናቶች ያረጋግጣሉ። ሰብስብ ካለ አገላለጽ የመልካም አስተዳደር ሥነምግባርና የጠንካራ ማኅበራዊ  እሴቶች ፀረ የሆነው ሙስና ነፃና ፍትሐዊ የገበያ ውድድርን የሚያዛባ፤ የኢንቨስትመንት መስፋፋትና መጐልበትን የሚገድብ፣ ለፍትህ መጓደል በር የሚከፍትና ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር፤ የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ሂደትን የሚያቀጭጭ ድህነትን በማባባስ ሰላምና መረጋጋት እንዳይሰፍን ጫና  የሚፈጥር፤ በመንግሥት በሕዝቦችና በተቋማት መካከልም መተማመንና የጋራ መተሳሰብ እንዳይኖር እንቅፋት የሚፈጥር  የሰው ልጆች የሰላምና የዕድገት ነቀርሳና ፀር ተደርጐ የሚወሰድ ነው።

በአገራችን ተጨባጭ ሁኔታም በፈጣን የዕድገት ሂደት ውስጥ መገኘታችንን ተከትሎ ከከተማ መሬት፣ከግብርና ታክስ ከግዢ ሂደትና  ከኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ ጋር በተያያዘ በከፍተኛ ደረጃ የሚገለጽ የሙስና ወንጀል እየተበራከተ መጥቷል ለማለት ያስደፍራል።

ከእዚህ አንፃር ድህነትን ለማስወገድ የሚደረገው እልህ አስጨራሽ ትግልና ትንቅንቅ በሙስና ወንጀል ምክንያት እንዳይስተጓጐል የፀረ ሙስና ትግላችን በየፈርጅና በየደረጃው  ተጠናክሮ መቀጠል እንደሚኖርበት የሚያጠያይቅ አይደለም። ከዓመታት በፊት በአገራችን የፀረ ሙስና ቀን «ሙስናን መዋጋት ድህነትን መዋጋት ነው» በሚል መርህ የመከበሩ እውነታም ለአገራችንና ለሕዝቦችዋ ከድህነት የከፋ ጠላት እንደሌላቸው የሚያሳይ ከመሆኑም በላይ የልማት ፀር የሆነውን ሙስና መታገልና በፅኑ የዓላማ ቁርጠኝነት መዋጋት እንደ የሕልውና ጉዳይ የሚወሰድ ስለመሆኑ ያስገነዝበናል።

በኢትዮጵያ  ሙስናና ተያያዥ ወንጀሎችን ለመከላከልና ብልሹ አሠራርንና አድልዎን የማይሸክም ኅብረተሰብ በመገንባቱ ሂደት ውስጥ ዓይነተኛ ሚና በመጫወት ላይ የሚገኘው የፌዴራል ሥነ -ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን በየጊዜው የሚያወጣቸው ሪፖርቶችና ከሚያስወስዳቸው ርምጃዎች ለመረዳት እንደሚቻለው ወንጀሉ የቱን ያህል እየሰፋና ሥር እየሰደደ መምጣቱን መገንዘብ ይቻላል።  በ2005 በጀት ዓመት በ10 ወራት ውስጥ በሙሰኞች የተመዘበረ 21 ሚሊዮን ብር 1945 ካሬ ሜትር መሬት አራት ሕንፃዎችና ሌሎች ንብረቶች የመመለሳቸው እውነታም ጥሩ ሐቁን የበለጠ ያጠናክረዋል። በተጨማሪም የተጠርጣሪዎችን ንብረት ማሳገድ በተመለከተ 128ሺ 709 ካሬ ሜትር፣ መሬት 28 ተሽከርካሪዎች፣  60 መኖሪያ ቤቶች፣  10 ድርጅቶች፣ 2.8 ሚሊዮን ብርና፣ 15 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር በፍርድ ቤት የመታገዳቸው ዜና፤ ከኮሚሽኑ ጥፋተኛ የማሰኘት አቅም እየተጠናከረ ከመምጣቱ አኳያ ሲመዘን የችግሩ ስፋትና አሳሳቢነት ጉልህ ያደርገዋል።

ሰሞኑንም ኮሚሽኑ ከሕዝብ የተቀበላቸውን ጥቆማዎች መሠረት በማድረግ ከብሔራዊ የመረጃ አገልግሎት ጋር ያካሄደውን ጥናትና ክትትል መሠረት አድርጐ በቂ የሰውና የሰነድ መረጃዎች አሰባስቦ ሁለት ከፍተኛ ባለሥልጣናትን ጨምሮ 12 ተጠርጣሪ ግለሰቦችን በፖሊስ ቁጥጥር ስር እንዲውሉ ማድረጉ፣  በአንድ በኩል የፀረ ሙስና ትግሉ እየከረረ መምጣቱን እንዲሁም ሙሰኞችን ለመፋረድ ከተያዘው አገራዊ ጠንካራ አቋም ማፈግፈግ የማይታሰብ ስለመሆኑ የሚያረጋግጥ ነው።

በአጠቃላይ ለልማታዊና ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እውን መሆን ለሕግ የበላይነት መከበር፤  ለሰላምና መረጋጋት ለመልካም አስተዳደርና ለነፃ ገበያ ሥርዓት መስፈን ፤እንቅፋትና ፀር የሆነውን የሙስና ወንጀል ማስወገድና መከላከል የሕልውና ጉዳይ በመሆኑ ሙሰኞችን በሕግ አግባብ ለፍርድ የማቅረቡ ሂደት ተጠናክሮ መቀጠል ይገባዋል። አገራችን የሙስና ወንጀል ፈጻሚዎችና ተባባሪዎቻቸውን ለአፍታም ቢሆን የምትታገስበትና የምትሸከምበት አቅም እንደሌላትም መታወቅ ይኖርበታል።
አዲስ ዘመን ጋዜጣ

No comments:

Post a Comment