Saturday, September 01, 2012

በመጨረሻው ስንብት ማግስት

(Sept 01, 2012, Addis Ababa, በጋዜጣው ሪፖርተር)--ነሐሴ 15 ቀን 2004 ዓ.ም. ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተው እሑድ ነሐሴ 27 ቀን 2004 ዓ.ም. ሥርዓተ ቀብራቸው በክብር በብሔራዊ ደረጃ የተፈጸመው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ፣ በኢትዮጵያ ሕዝብና በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ የመጨረሻ ስንብት ተደርጎላቸዋል፡፡ በሕዝባቸውና በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ “ባለ ራዕዩ መሪ” ተብለው የተወደሱት ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ በመሪር ሐዘን ተሸኝተዋል፡፡ የበርካታ አገር መሪዎች፣ የመንግሥታት ተወካዮችና የዓለም አቀፍ ድርጅቶች መሪዎች፣ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍል ተወካዮች፣ ወዳጆቻቸው፣ ዘመዶቻቸውና ቤተሰቦቻቸው በተገኙበት በመንበረ ፀባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል አስከሬናቸው በክብር አርፏል፡፡

Picture: Mediafax
ላለፉት 13 ቀናት በብሔራዊ ሐዘን ውስጥ የከረሙት ሕዝብና መንግሥት የጠቅላይ ሚኒስትሩን አስከሬን በክብር ካሳረፉ በኋላ መደበኛ ተግባራቸውን እንደሚቀጥሉ ይጠበቃል፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትሩ እግር ተተክተው የሚሰየሙት አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር በፓርላማ ይሁንታ እንደሚያገኙ ሲጠበቅ፣ ለቀናት ተቀዛቅዞ የነበረው የሥራ እንቅስቃሴ በሙሉ ኃይል እንደሚጀመር ይታሰባል፡፡ ያለ ምንም ኮሽታና ፍፁም በሆነ ሰላማዊ ድባብ ውስጥ የተጠናቀቀው የሐዘንና የቀብር ሥነ ሥርዓት ወቅት፣ በተረጋጋና በአዲስ የመነሳሳት ስሜት ሰላማዊ ሆኖ እንደሚቀጥል የመንግሥት ባለሥልጣናት እየተናገሩ ነው፡፡

እሑድ ዕለት የጠቅላይ ሚኒስትሩ የቀብር ሥነ ሥርዓት በከፍተኛ ድምቀት ሲከናወን፣ በአዲስ አበባና በተለያዩ ክልሎች የሚገኙ ዜጎች ሥነ ሥርዓቱን በትላልቅ ስክሪኖችና በቴሌቪዥን ቀጥታ ሥርጭት ተከታትለዋል፡፡ በታላቁ ቤተ መንግሥት በአካል በመገኘትና በያሉበት ቦታ ሆነው ሐዘናቸውን በተለያየ መንገድ ለገለጹ ዜጎች መንግሥት ምስጋና ያቀረበ ሲሆን፣ ይህ ዓይነቱ አንድነት ወደፊትም ተጠናክሮ ይቀጥል ዘንድ ጥሪ አቅርቧል፡፡

ከሕልፈታቸው በኋላ ተክለ ሰብዕናቸው የገዘፈው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ያስጀመሯቸውን ትላልቅ የልማት ውጥኖች ለማስፈጸም ርብርብ እንደሚደረግ ከየአቅጣጫው እየተነገረ ሲሆን፣ ይህንን ቃል ለማስፈጸም አዲሱ አመራር ምን ያህል ዝግጁ ነው የሚለው ጥያቄም እያነጋገረ ነው፡፡ አመራሩ ከዝግጁነቱ በተጨማሪ አገርን የመምራትና ፖሊሲዎችን የማስፈጸም ችሎታውም እንዲሁ በሕዝቡ ውስጥ መነጋገሪያ ሆኗል፡፡ በማይታክትና በማይደክም ሰብዕና የሚገለጹትን ጠቅላይ ሚኒስትር በብቃት በመተካት የልማት አጀንዳዎችን ማስፈጸም፣ የዲሞክራሲና የሰብዓዊ መብቶችን ማስከበር፣ የአገሪቱን የግዛት አንድነት ማረጋገጥ፣ ሰላምና መረጋጋት ማስፈን፣ በአፍሪካና በዓለም አደባባይ የኢትዮጵያንን የመሪነት ሚና ማስቀጠል መቻል፣ በአፍሪካ ቀንድ የተረጋጋችና ጠንካራ አገር ሆና መቀጠሏን ማረጋገጥ፣ ወዘተ የሚሉትም ይጠቀሳሉ፡፡

ከመለስ ሕልፈት በኋላ አለመረጋጋት ሊኖር ይችላል፣ የሥልጣን ሽኩቻ ይፈጠራል፣ የአፍሪካ ቀንድ ይተራመሳል፣ የተጀመሩት የልማት ሥራዎች ይሰናከላሉ፣ የሕግ የበላይነት አይኖርም፣ የብሔሮች ብጥብጥ ሊኖር ይችላል፣ ወዘተ ለሚባሉ መላምቶችና ግምቶች እስካሁን መንግሥት በይፋ ምላሽ ባይሰጥም፣ እንዲህ ዓይነቶቹን አባባሎች ፉርሽ የሚያደርግ ውስጣዊ አንድነት መኖሩንና ይህም በተግባር እንደሚታይ ውስጥ አዋቂዎች በራስ መተማመን እየገለጹ ነው፡፡ በመለስ ሕልፈት ወደር የሌለው ቁጭት ያደረባቸው ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት ብቁና ቀልጣፋ የቡድን አመራር ለመስጠት ዝግጅታቸውን ማጠናቀቃቸው ይነገራል፡፡

ባለፈው ዓርብ ለኬንያው ዴይሊ ኔሽን መግለጫ የሰጡት በኬንያ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሸምሰዲን አህመድ ሮበሌ ያረጋገጡትም ይህንን ነው፡፡ እሳቸው እንዳሉት ኢትዮጵያ ሰላማዊ የሥልጣን ሽግግር ለማድረግ ለዓለም ማረጋገጫዋን ሰጥታለች፡፡ ፖለቲካዊ መተካካቱ ሰላማዊ በሆነ መንገድ በአገሪቱ ሕገ መንግሥት መሠረት እየተከናወነ መሆኑንም አስረድተዋል፡፡ ከጠቅላይ ሚኒስትር መለስ የቀብር ሥነ ሥርዓት በኋላ ፓርላማው ተሰብስቦ አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝን ተተኪው ጠቅላይ ሚኒስትር እንደሚያደርጋቸው እንደገና ማረጋገጫ ሰጥተዋል፡፡ ኢትዮጵያም የተረጋጋችና በአካባቢው ጠንካራ አገር ሆና ትቀጥላለች ሲሉ ገልጸዋል፡፡

በሐዘኑ ወቅት ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት በተለያዩ ጉዳዮች በመወጠራቸው ምክንያት ማነጋገር ባይቻልም፣ ለባለሥልጣናቱ በቅርበት ያላቸው ምንጮች እንደሚሉት፣ ለራሳቸው ሕይወት ምንም ሳይሰስቱ ያላቸውን ሁሉ በመስጠት ሰማዕት ለሆኑት መሪያቸው  ክብር ሲሉ ማንኛውንም መስዋዕትነት ለመክፈል ዝግጁ ሆነዋል፡፡ ከመለስ በኋላ አለመረጋጋትና መከፋፈል ይፈጠራል የሚሉ ወገኖችን ትንቢት ተረት ለማድረግ መነሳታቸውን እነዚህ ምንጮች በእርግጠኝነት ይናገራሉ፡፡ የመለስ ሕልፈት ከተነገረ ጊዜ ጀምሮ አገሪቷ ፍፁም ሰላማዊ ሆና መሰንበቷ ይህንን ያረጋግጣል ይላሉ፡፡ ይህንን ሰላማዊ ድባብ በተጠናከረ ሁኔታ ለማስቀጠል አመራሩ ቁርጠኛ ነው በማለትም ያክላሉ፡፡

በጠቅላይ ሚኒስትሩ ሕልፈት ምክንያት ምንም የተለየ ሁኔታ እንደማይኖር የሚናገሩት ምንጮች፣ ገዥው ፓርቲ ኢሕአዴግ የሚመራው መንግሥት ከወትሮው የተለየ አዲስ ነገር አያስተዋውቅም ይላሉ፡፡ ይልቁንም በጠቅላይ ሚኒስትሩ አመራር እዚህ የደረሰው ፌዴራላዊ ሥርዓት በተጠናከረ ሁኔታ ይቀጥላል፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካይነት ሲከናወኑ የነበሩ ሥራዎች በሙሉ የገዥው ፓርቲ ዕቅዶች በመሆናቸው ጉዞው እንደነበረው ይቀጥላል በማለት አስረግጠው ይገልጻሉ፡፡

የአገር መከላከያ ሠራዊትና የፖሊስ አባላት፣ የፀጥታና የደኅንነት ተቋማት ከምንጊዜውም በላቀ ሁኔታ የአገር ሉዓላዊነትን በማስከበርና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን በመጠበቅ ወደር የሌለው ተግባር እያከናወኑ መሆናቸውን የሚገልጹት ምንጮች፣ ኢትዮጵያ በታሪኳ አይታው የማታውቀው ሰላማዊ ፖለቲካዊ መተካካት በሚያስደንቅ ሁኔታ ይከናወናል በማለት በእርግጠኝነት ይናገራሉ፡፡ እያንዳንዱ ጉዳይ የሚከናወነው በሕገ መንግሥቱ መሠረት ብቻ ነው በማለትም ያስረዳሉ፡፡

ከጠቅላይ ሚኒስትር መለስ የቀብር ሥነ ሥርዓት በኋላ የአገሪቱ ፓርላማ ስብሰባ የሚጠራ ሲሆን፣ ተተኪው ጠቅላይ ሚኒስትር በገዢው ፓርቲ አባላት ተጠቁሞ ይሁንታ እንደሚሰጠው ሲጠበቅ፣ አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ምክትሉን በማቅረብ ያፀድቃል፡፡ በመለስ የመጨረሻ ስንብት ማግስት የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች የሕዝቡን ትኩረት እንደሚስቡ ብዙዎች ይናገራሉ፡፡ የድኅረ መለስ ኢትዮጵያን እንቅስቃሴ የኢትዮጵያ ሕዝብ ብቻ ሳይሆን የአፍሪካና የዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ ጭምር በከፍተኛ ትኩረት የሚከታተሉት መሆኑን በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ተነባቢነት ያላቸው ሚዲያዎች በመግለጽ ላይ ናቸው፡፡

በተለይ በዓለም አቀፍ ሚዲያዎች ላይ የተለያዩ አስተያየቶችን የሚሰነዝሩ የፖለቲካ ተንታኞችና ጋዜጠኞች ከመለስ ሕልፈት በኋላ ያለመረጋጋት ሥጋቶች እንደሚኖሩ በስፋት ማተታቸውን በተመለከተ ምላሽ የሚሰጡት ምንጮች፣ የብዙዎቹ አስተያየት የአገሪቱን ነባራዊ ሁኔታ በጥልቀት ካለመረዳትና የገዥውን ፓርቲ አባላትና አመራር ውስጣዊ አንድነት ካለመወቅ ነው በማለት ይከራከራሉ፡፡ ብዙዎቹ አስተያየቶችም ጥልቀት የሌላቸውና ሌላው ቀርቶ ኢትዮጵያንና ሕዝቧን በሚገባ አለማወቃቸውን ያሳያል ሲሉ ይከራከራሉ፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩን መተካት ከባድ ቢሆንም አመራሩ በጋራ በመሆን ይኼንን ግዳጅ እንደሚወጣ የሚናገሩት እነዚሁ ምንጮች፣ በበርካታ ሚዲያዎች የሚቀርቡት ትንታኔዎችና ትንበያዎች አሁን ያለውን ድባብ እንኳን አይገልጹትም ይላሉ፡፡ በተለይ ገዥው ፓርቲ አገርን ለመምራት የሚችሉ በርካታ በሳል ሰዎች እንዳሉት በማስታወስ፣ አሁን የአገሪቱን አመራር ለመረከብ የተዘጋጁት አቶ ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በመተካካቱ ሒደት ውስጥ በርካታ ልምዶችን መቅሰማቸውን ያስታውሳሉ፡፡ ለእንዲህ ዓይነቱ አመራር ሰጪነት በብቃት ከመዘጋጀታቸውም በተጨማሪ ከሌሎች አመራሮች ጋር በመሆን የተሻለ ውጤት ማስመዝገብ የሚችሉበት ደረጃ ላይ ናቸው ይላሉ፡፡ እንደ ቡድን ደግሞ በጠቅላላ አመራሩ አሁን ከሚታየው በላይ እጥፍ ድርብ ውጤት ለማስመዝገብ በከፍተኛ እልህና ወኔ ለመረባረብ ራሳቸውን ማዘጋጀታቸውን በእርግጠኝነት ያስረዳሉ፡፡

መንግሥት ከፊቱ የሚጠብቁት በርካታ ሥራዎች አሉት በማለት፣ እነዚህን ሥራዎች በብቃት በማከናወንና ቀደም ሲል እንደ ችግር የሚጠቀሱ ጉድለቶችን በማስተካከል አገራዊ አደራውን በብቃት ለመወጣት ተዘጋጅተዋል ሲሉ ያስረዳሉ፡፡ ኢትዮጵያ አሁንም በዓለም አቀፍና በአኅጉር ደረጃ የመሪነት ሚናዋን መጫወቷን እንደምትቀጥል፣ የአፍሪካ ቀንድን የማረጋጋት ሥራዋን እንደ ወትሮው እንደምታከናውን፣ የሕዝቡን አንድነት በማስጠበቅ ዲሞክራሲያዊ ሥርዓቱን በስፋትና በምልዓት እንደምታረጋግጥ አመራሩ የጋራ አቋም እንዳለው ምንጮች አስታውቀዋል፡፡ ከምንም ነገር በላይ ግን በኢትዮጵያና በኢትዮጵያዊያን ብሔራዊ ጥቅም ላይ ድርድር እንደማይደረግ ዓለም ካሁኑ እንዲያውቀው እንደሚደረግ በሙሉ ልብ አስረድተዋል፡፡ 
Source: Reporter

Related topics:
በጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ የቀብር ሥነ ሥርዓት ላይ ለመገኘት የበርካታ አገራት መሪዎች አዲስ አበባ እየገቡ ነው 
በመለስ ሽኝት ዋዜማ 
ባራክ ኦባማ በጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ሥርዓተ ቀብር የሚገኝ ቡድን እንደሚልኩ አስታወቁ 
በደቡብ አፍሪካ የሚገኙ ኤርትራውያን የኅዘን መግለጫ አስተላለፉ 
የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ስርዓተ ቀብር ዛሬ ተፈፀመ 
ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ አረፉ 
የጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ሥርዓተ ቀብር እስከሚፈጸም ድረስ በመላው አገሪቱ ብሔራዊ የሐዘን ቀን ሆኖ ይቆያል  

No comments:

Post a Comment